በበባህር ዳር ከተማ የሚታው የነዳጅ ችግር ተባብሶ ቀጥሏል፡፡

ታኀሳስ (ስምንት) ቀን ፳፻፯ / ኢሳት ዜና :-ሰሞኑን እንደ ሌሎች የሃገሪቱ ክፍሎች በነዳጅ አቅርቦት ሲቸገሩ የቆዩት የባህርዳር የታክሲና ባጃጅ አሽከርካሪዎች ዛሬም ድረስ ችግሩ ተባብሶ መቀጠሉን ለዘጋቢያችን ተናግረዋል።

በትናንትናውና በዛሬው እለት በከተማዋ ካሉት ከአስር በላይ ማደያዎች በአንዱ ብቻ ነዳጅ የሚገኝ መሆኑን የተናገሩት አሽከርካሪዎች ፣ በዚህ ነዳጅ ማደያ ለመቅዳት እስከ ሁለት መቶ ሜትር ተሰልፈው ለሰዕታት እንደሚቆዩ ተናግረዋል፡፡

ሁል ጊዜ በወሩ መጨረሻ የነዳጅ ዋጋ ማሻሻያ ይደረጋል በማለት ማደያዎች ከንግድና ኢንዱስትሪ ባለሙያዎች ጋር በሚያደርጉት የውስጥ ስምምነት በተገልጋዩ ላይ እጥረት እንደሚፈጥሩ አሽከርካሪዎች ተናግረዋል፡፡

ባለማደያዎቹ በበኩላቸው መንግስት ያደረገው የዋጋ ማሻሻያ እንደማያዋጣቸው ይናገራሉ። በነዳጅ እጥረት ሳቢያ መንገደኞች ከፍተኛ መንገላታት እየደረሰባቸው መሆኑን ይገልጻሉ።