በቁጫ ወረዳ ከማንነት ጥያቄ ጋር በተያያዘ የታሰሩት ሰዎች ፍትህ አጥተው በእስር ላይ ናቸው

ሚያዝያ፩(አንድ ) ቀን ፳፻፯ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- በጋሞጎፋ ዞን በቁጫ ወረዳ ከሁለት አመታት በፊት ጀምሮ የተነሳውን የማንነት  ጥያቄ መርታችሁዋል በሚል የተያዙት ከ150 በላይ የከተማዋ ነዋሪዎች ፍርድ ሳይሰጣቸው በአርባ ምንጭ እስር ቤት በመሰቃየት ላይ ናቸው።

ፍትህ አጥተው ከታሰሩት መካከል አንድ ሰው በህክምና እጦት ህይወቱ ማለፉን ኢሳት መዘገቡ ይታወሳል። በአካባቢው የተነሳውን ግጭት ተከትሎ በሺዎች የሚቆጠሩ ዜጎች ቀያቸውን ለቀው ተሰደዋል። ካለፉት ሳምንታት ጀምሮ ደግሞ በሰላምበር ከተማ ከ140 በላይ አርሶአደሮች ከመሬታቸው እንዲፈናቀሉ ተደርጎ መሬት አልባ መሆናቸውን የኢሳት የአካባቢው ምንጮች ተናግረዋል። አርሰዎ አደሮቹ መሬታቸው ለከተማ ማስፋፋት እንደሚፈለግ የተነገራቸው ቢሆንም፣ ተተኪ መሬት ሳይሰጣቸው ከይዞታቸው ተነስተው መጠለያ አልባ ሆነው እንደሚገኙ ነዋሪዎች ተናግረዋል።