በሩሲያ ሆስፒታል ውስጥ በተነሳ የእሳት አደጋ 37 ሰዎች ሞቱ

መስከረም ፫(ሦስት)ቀን ፳፻፮ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-በሰሜን ምዕራብ ሩሲያ በሚገኝ በ አንዳ ሳይካተሪክ ሆስፒታል ውስጥ በተነሳ የ እሳት አደጋ 37 ሰዎች መሞታቸውን  ባለስልጣናት ገለጹ።

“ኖቭጎሮድ” ተብሎ በሚጠራው ግዛት በ”ሉካ” መንደር ውስጥ ከእንጨት በተሠራው ሆስፒታል ውስጥ ወደ 60 ሰዎች እየታከሙ ነበር።

የሩሲያ ብዙሀን መገናኛ ሪፖርቶችን በመጥቀስ ቢቢሲ እንዳለው፤ ህሙማኑን ትንከባከብ የነበረች አንዲት ነርስም ከሟቾቹ መካከል ትገኝበታለች።

እስካሁን ከሟቾቹ መካከል የ15ቱ  አስከሬን መገኘቱም ተመልክቷል።

እሳቱ የተነሳው እንደ አውሮፓውያን ሰ ዓት አቆጣጠር ከምሽቱ 23 ሰ ዓት ላይ ሲሆን፤ አደጋው  ከህሙማኑ መካከል ሲጃራ በሚያጨስ ታካሚ ሳይነሳ እንዳልቀረ ተገምቷል።

እሳቱ በመጀመሪያ ወንዶች ተኝተው ከሚታከሙበት ክፍል በመነሳት “ኦክሶቺ”  ሆስፒታልን በፍጥነት እንዳዳረሰው  የአደጋ ሚኒስቴር ባለስልጣናት ተናግረዋል።

መጀመሪያ ላይ  አንድ ታማሚ እንደተኛ በእሳት እየተቃጠለ ማየቱን የተናገረው  የሀኪም ቤቱ ሠራተኛ፤ ታማሚው ለዚያ የተዳረገው በአልጋው ላይ እያለ ሲጃራ ሲያጨስ ሳይሆን እንዳልቀረ ግምቱን ተናግሯል።

ታማሚው በተኛበት ክፍል መደዳ  ያሉት ክፍሎች እጅግ በጠና የተጎዱ ህሙማን ተኝተው የሚታከሙባቸው እንደነበሩ የሐኪም ቤቱ ሠራተኛ ጨምሮ ገልጿል።