በሞያሌ በተነሳው ተቃውሞ ከገዢው ፓርቲ ጋር ግንኙነት አላቸው የተባሉ ሆቴሎች ከፍተኛ ውድመት ደረሰባቸው

ሚያዝያ ፯ (ሰባት) ቀን ፳፻፯ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- የከተማ ነዋሪዎች ለኢሳት እንደገለጹት በከተማዋ ከሚታወቁት  ሆቴሎች መካከል  ፈቃዱ ሆቴል ፣ ኢትዮ ኬኒያ ሆቴል ፣ ሃጎስ ሆቴልና ማሕሌት ሆቴል ጉዳት ድርሶባቸዋል።

የሆቴሉ ባለቤቶች የገዢው ፓርቲ ደጋፊዎች ናቸው በሚል ጥቃት እንደተፈጸመባቸው ነዋሪዎች ተናግረዋል። በተለይ ኢህአዴግን በመደገፍ እና ቅስቀሳ በማድረግ የሚታወቁት የማህሌት ሆቴል ባለቤት ንብረት ከፍተኛ ጉዳት ደርሶበታል።  የአካባቢው ሽማግሌዎችና የጎሳ መሪዎች የተጎዱ ሆቴሎችን የጎበኙ ሲሆን ፣መረጋጋት እንዲፈጠር ነዋሪዎች ለማሳመን እየጣሩ ነው።

ከሞያሌ ወጣብላ በምትገኘው ኩሌንሳ መንደር የተኩስ ድምጽ መሰማቱን የገለጹት ምንጮች፣ ውጥረቱ አሁንም ድረስ እንዳለ ተናግረዋል። በመከላከያ ሰራዊት አባላትን በሶማሊ ክልል ታጣቂዎች መካከል የተነሳው ግጭት በፌደራል ፖሊሶች ጣልቃ ገብነት ቢበርድም፣ በማንኛውም ጊዜ ሊነሳ ይችላል በሚል ነዋሪዎች ስጋታቸውን ገልጸዋል። ትምህርት ቤቶች፣ የመንግስት መስሪያ ቤቶችና አንዳንድ ድርጅቶች ዛሬ መከፈታቸውን ለማወቅ ተችሎአል።