በሙስና የታሰሩት የጉምሩክ አቃቤ ሕግ፣ ቀብረውት የነበረ ከ1ሚልዪን በላይ ብር መገኘቱ ተነገረ

ሰኔ ፫ (ሦስት) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም

ኢሳት ዜና:-በሙስና ተጠርጥረው በማረሚያ ቤት የሚገኙት የገቢዎችና ጉምሩክ ባለሥልጣን ዓቃቤ ህግ ምክትል ዳይሬክተር አቶ ማርክነህ አለማየሁ ቀብረውታል የተባለ ከአንድ ሚልዮን ብር በላይ መገኘቱ ታውቋል።

ጉዳዪን የሚከታተለው የምርመራ ቡድን እንዳስታወቀው ከሆነ፣- አቶ ማርክነህ አለማየሁ በወንድማቸው አማካኝነት ለመሰወር አቅደው የቀበሩት አንድ ሚሊዮን ሶስት መቶ ዘጠና ሺ ብር የተገኘው ወላይታ ሶዶ፣ ወራንዛላሸ በተሰኘች ቀበሌ ገበሬ ማህበር ውስጥ ነው።

ይኸው ገንዘብ ተገኘ የተባለው ግንቦት 30 ቀን 2005 ዓ.ም  ነው።  ገንዘቡ አቶ ማርክነህ በኃላፊነት ሲሰሩ በነበሩበት ወቅት በወንጀል የተጠረጠሩ ግለሰቦች ላይ ክስ ባለመመስረት፣ እንዲሁም መከፈል የሚገባቸውን የመንግሥት ገቢ እንዳያስገቡ በመመሳጠር የሰበሰቡት ነው» በማለት የምርመራ ቡድኑ አስታውቋል።ካሁን ቀደም የፌዴራል ገቢዎችና ጉምሩክ ባለስልጣን ምክትል ዳይሬክተር በሆኑት አቶ ገብረዋህድ ገብረጊዮርጊስ መኖሪያ ቤት ዉስጥ፣ 200ሺ የኢትዮጵያ ብር፤ 26ሺ ዩሮ፤ ፓዉንድና የተለያዩ አገራት የገንዘብ ኖቶች፤ መገኘቱ ይታወሳል።
በአቶ መላኩ ፈንታ መዝገብ 3ኛው ተከሳሽ የሆኑት አቃቤ ሕግ ማርክነህ አለማየሁ የታሰሩት፣ ከአንደኛው ተከሳሽ አቶ መላኩ ፈንታ እና ከሁለተኛው ተከሳሽ አቶ እሸቱ ወልደሰማያት ጋር በማበር፣- ሕገ-ወጥ ጥቅም ለማግኘት ሲባል በ2001 ዓ.ም በአራጣ ብድር በፍርድ ቤት የተመሰረተን ክስ በስልጣናቸው እንዲቋረጥ አድርገዋል በሚል ተጠርጥረው ነው። መርማሪ ቡድኑ አገኘሁ ያለውን ገንዘብ ከገለልተኛ ወገን ማጣራት አልተቻለም።