በሙስና ወንጀል ተጠርጥረው ከታሰሩት መካከል የአቶ አባይ ጸሃዬ ባለቤት አንዷ ናቸው ተባለ

በሙስና ወንጀል ተጠርጥረው ከታሰሩት መካከል የአቶ አባይ ጸሃዬ ባለቤት አንዷ ናቸው ተባለ

(ኢሳት ዜና –ሐምሌ 21/2009) በሙስና ወንጀል ተጠርጥረው ከታሰሩት መካከል የአቶ አባይ ጸሃዬ ባለቤት እንደሚገኙበት ታወቀ።

ሌሎች አራት ሰዎችም ከሙስና ወንጀል ጋር በተያያዘ በቁጥጥር ስር ውለዋል።

የደህንነት ምንጮች እንደገለጹት የአቶ አባይ ጸሃዬ ባለቤት ወይዘሮ ሳሌም ከበደ በቁጥጥር ስር የዋሉት ለልጃቸው መልስ በዝግጅት ላይ እንዳሉ ነበር።

አቶ አባይ ጸሃዬ በኢትዮጵያ ስኳር ኮርፖሬሽን ዋና ዳይሬክተር እያሉ ባከነ ከተባለው 77 ቢሊየን ብር ጋር በተያየዘ ስማቸው በተደጋጋሚ ይነሳል ።

ይህ በእንዲህ እንዳለም በሙስና ወንጀል ተጠርጥረው ከታሰሩት መካከል የአቶ አባይ ጸሃዬ ባለቤት እንደሚገኙበት እየተነገረ ነው ።

ከአቶ አባይ ጸሃዬ ጋር ከፍተኛ ቅርበትና የንግድ ሽርክና አላቸው የሚባሉት አቶ የማነ ግርማይም በቁጥጥር ስር ውለዋል።

የማነ ግርማይ የባቱ ኮንስትራክሽኝ ባለቤት መሆናቸውም ታውቋል።

በቀዳሚነት ከተያዙት 34 የሙስና ተጠርጣሪዎች ጋር የታሰሩት ወይዘሮ ሳሌም ከበደ የአቶ አባይ ጸሃዬ ባለቤት ሲሆኑ ከኦሞ ኩራዝ 5 የስኳር ፕሮጀክት ጋር በተያያዘ መታሰራቸው ታውቋል። የባቱ ኮንስትራክሽን ባለቤት አቶ የማነ ግርማይም ከዚሁ ጋር በተያየዘ መታሰራቸው ይታወቃል።

በሙስና ሰዎች መታሰራቸው ይፋ የተደረገው ማክሰኞ ሃምሌ 18 2009 ሲሆን ሴትዬዋ በቁጥጥር ስር የዋሉት ሰኞ ሐምሌ 17/2009 እንደሆነም መረጃዎች አመልክተዋል።

ከቅርብ አመታት ወዲህ ከአቶ አባይ ጸሃዬ ጋር ተጣምረው በአንድ ጎጆ በመኖር ላይ የሚገኙት ወይዘሮ ሳሌም ከበደ ቅዳሜ ሐምሌ 15/2009 ከቀድሞ ትዳራቸው ያፈሩትን ልጃቸውን በአዲስ አበባ ሒልተን ሆቴል ደግሰው የዳሩ ሲሆን፣አቶ አባይ ጸሃዬ ጋርም በሰርጉ ላይ ተገኝተዋል።

የመልሱ ፕሮግራም ካዛንቺስ በሚገኘው ኢንተር ኮንቲነንታል ሆቴል ሰኞ ሐምሌ 17/2009 የተዘጋጀ ቢሆንም ወይዘሮ ሳሌም ከበደ በእለቱ ከመልሱ ዝግጅት በፊት በቁጥጥር ስር ውለዋል።

አቶ አባይ ጸሃዬ ባለቤታቸው ከታሰሩ በኋላ የመልስ ፕሮግራሙ ላይ መገኘታቸውንም የደህንነት ምንጮች ገልጸዋል።

ርምጃው እስከ አቶ አባይ ጸሐዬ ይዝለቅ አይዝለቅ ግን የታወቀ ነገር የለም። በርሳቸው ዙሪያ ያሉትን ማሰሩ ግን ለርሳቸው ግልጽ መልእክት እንደሆነም ተመልክቷል።

ርምጃው አቶ አባይ ጸሃዬ ላይ ያልቀጠለው በአንድ በኩል የፓርላማ አባል በመሆናቸው ያለመከሰስ መብታቸው ባለመነሳቱ እንደሆነ የሚገምቱ አሉ። በሌላም በኩል ርምጃው እሳቸውን ከማስፈራራት ያለፈ እንዳልሆነም ተመልክቷል።

እስራቱን የጀመረው ወገን በርምጃው ከቀጠለና አቶ አባይ ጸሐይን ማሰር ከወሰነ ፓርላማውን አስቸኳይ ስብሰባ ጠርቶ ያለመከሰስ መብታቸውን ማነሳት ይኖርበታል።

የውስጥ ምንጮች እንደሚሉት ከሆነ ግን አቶ አባይ ጸሃዬን ለማስፈራራት እንጂ ለማሰር አቋም አልወሰደም።

አቶ አባይ ጸሃዬ ከኢትዮጵያ ስኳር ኮርፖሬሽን የ77 ቢሊየን ብር ፕሮጀክት ጋር በተያያዘ በርካታ ቢሊየን ብር በማባከን የሚጠቀሱ በሀገሪቱ በግንባር ቀደም ሙሰኝነት የተቀመጡ ቢሆንም በፖለቲካ አሰላለፋቸው የበላይነቱን ወደ ያዘው ቡድን ከተጠጉ ላይጠየቁም ይችላሉ።

በሙስና ወንጀል ውስጥ እጃቸው አለበት የተባሉና ስማቸው ያልተገለጸ ሌሎች አራት ሰዎችም በቁጥጥር ስር ውለዋል ተብሏል።