በመጪው  የጥምቀት በዓል ወጣቶች ሰማያዊ ቲሸርቶችን  መልበስ አትችሉም ተባሉ፤ 

ጥር ፩(አንድ) ቀን ፳፻፯ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-በቲሸርቶቹ ላይ የሚያሳትሟቸውን ሀይማኖታዊ  ጥቅሶችም  በራሳቸው መምረጥ እንደማይችሉ ተነገሩ። ድርጊቱ  የግል የማመን መብታችንን የሚጋፋ ከመገሆኑም በላይ ሀይማኖታችንንም መድፈር ነው ያሉ ወጣቶች ቁጣቸውን በመግለጽ ላይ ይገኛሉ።

ፖሊሶች ከትናት ታህሳስ 1 ቀን ጀምሮ በ አዲስ አበባ የተለያዩ ሰፈሮች በመንቀሳቀስ ወጣቶች  ለመጪው የከተራ እና የጥምቀት በዓል ሰማያዊ-ቲሸርት መልበስ እንደማይችሉ፣ እንዲሁም በቲሸርቶቻቸው ላይ የሚያሳትሟቸውን ሀይማኖታዊ ጥቅሶች  ፓሊሶች  እስከሚነግሯቸው ድረስ በራሳቸው ፍላጎት ማጻፍ እንደማይችሉ  በመቀስቀስ ላይ መሆናቸውን የቀበና፣ የምኒልክና የፈረንሳይ ሌጋሲዮን ወጣቶች ለኢሳት ገለጹ። ወጣቶቹ ሰማያዊ ቀለም ያለው ቲ-ሸርት መልበስ አትችሉም የተባሉበት ምክንያት በግልጽ ባይነገራቸውም፤ ጉዳዩ ከሰማያዊ ፓርቲ ጋር የተያያዘ ሳይሆን እንደማይቀር ግምታቸውን ተናግረዋል።

መቶ መቶ ብር በማዋጣት ለበዓሉ የምንለብሰውን ቲሸርት እያሰራን በምንገኙበት  ወቅት  መንግስት  የምንለብሰውን ቲ-ሸርትና በቲሸርታችን ላይ የምናጽፈውን ጥቅስ እኔ ነኝ የምመርጥላችሁ ማለቱ ዓይን ያወጣ አምባገነንነት ብቻ ሳይሆን ለምእመናን  ያለውን ንቀትም ጭምር  የሚያሳይ ነው ብለዋል-ወጣቶቹ። ፖሊሶች ከትናንት ጀምሮ  ቅስቀሳ እያደረጉ ቢሆንም፤  የየሰፈሩ ወጣቶች ሊቀበሏቸው አልቻሉም። ይልቁንም  በፖሊሶቹ ቅስቀሳ የተበሳጩ  ወጣቶች  ቁጣቸውን በመግለጽ ላይ ይገኛሉ። ሂጃብ መልበስ በመከልከሉ በርካታ ሙስሊሞች ተቃውሟቸውን እያሰሙ እንደሚገኙ ይታወቃል።