በመከላከያ አመራር ላይ ከፍተኛ ብወዛ እየተደረገ ነው

(ኢሳት ዜና–ሕዳር 15/2010) በኢትዮጵያ እየተባባሰ የመጣውን ውጥረት ተከትሎ በመከላከያ አመራር ላይ ከፍተኛ ብወዛ እየተደረገ መሆኑ ተሰማ።

ብወዛው በተለይ የኦሮሞና አማራ ተወላጆች ላይ የተነጣጠረ መሆኑንም ምንጮች ለኢሳት ገልጸዋል።

በጄኔራል መኮንኖች አካባቢ አመራሩ በሕወሃት ጄኔራሎች በመያዙ ብወዛው ከዚያ በመለስ ባለው የስልጣን መዋቅር ላይ ማተኮሩ ተመልክቷል።

በመከላከያ ሚኒስቴር ውስጥ በተጠናከረው ብወዛ በቅድሚያ የተሸጋሸጉ የ12 መኮንኖች ዝርዝር ለኢሳት ደርሶታል።

በዚህም መሰረት ኮለኔል አበራ ለማ፣ኮለኔል ሙሉ ዘውዴ እንዲሁም ሻለቃ ደጀኔ ጉርሙ ከሰራዊቱ አመራርነት ተነስተው ወደ ሎጅስቲክ ተዛውረዋል።

ሻለቃ ንጉሴ ኤጀርሳ፣ኮለኔል ደንቢ ገሪ፣እንዲሁም ኮለኔል ገረመው ሁንዴ ከሰራዊቱ አመራር ወደ ስልጠና ሲወሰዱ ኮለኔል ገዝሙ ደበላና ኮለኔል ሰለሞን ሁንዴ ወደ ምዕራብ እዝ አስተዳደር ክፍል ተሸኝተዋል።

ኮለኔል አለሙ ቅጣቴ በኬንያ በኤምባሲው ስር ካለው ስውር የደህንነት መዋቅር ወደ አዲስ አበባ ወታደራዊ ደህንነት ሲዛወሩ ኮለኔል አለሙ ጨከነ ከሰሜን ዕዝ ተነስተው በተመሳሳይ ወደ ወታደራዊ ደህንነት ተልከዋል።

ኮለኔል ስለሺ አሰፋና ኮለኔል አዱኛ ገርባ ከሰሜን ዕዝና ከማዕከላዊ ዕዝ የሰራዊቱ መደብ ተነስተው ወደ ትራንስፖርት ዘርፍ ተሸኝተዋል።

በተመሳሳይ ኮለኔል ጀማል ሳህሌ ከወታደራዊ ደህንነት ተነስተው ወደ ትራንስፖርት ተዛውረዋል።

ኮለኔል ቱሉ ኢርኮ ከወታደራዊ ዘመቻ መመሪያ ተነስተው ወደ ስታፍ ኮሌጅ ሲሔዱ ኮለኔል ቻሌ አየለም ከዘመቻ መምሪያ ወደ ሰላም ማስከበር ተዛውረዋል።

ብወዛው እንደሚጠናከርና በተዋረድም እንደሚቀጥል ከኢሳት ምንጮች ዘገባ መረዳት ተችሏል።

ከ20 አመት በፊት ሰራዊቱ ሲዋቀር ከፍተኛ የአዛዥነት ቦታዎች በትግራይ ተወላጆች ብቻ ተያዙ የሚል ተቃውሞ እንደነበር የሚታወስ ነው።

ሆኖም በሂደት ይስተካከላል የሚል ቃል መገባቱንም የሰራዊቱ አባላት ያስታውሳሉ።

ነገር ግን ከጊዜ ወደ ጊዜ የሰራዊቱን የአመራር ስፍራ ይበልጥ ወጥ እንዲሆን በትግራይ ተወላጆች የመሙላቱ ስራ ተጠናክሮ መቀጠሉ ሲዘገብ ቆይቷል።

በቅድሚያ ብርጋዴር ጄኔራል ሃይሌ ጥላሁን እንዲሁም ሜጀር ጄኔራል አባዱላ ገመዳን በጡረታና ወደ ሲቪል በማዛወር ወጥነቱን የማስፋቱ እንቅስቃሴ መጀመሩን የሚገልጹት የመከላከያ ምንጮች ከምርጫ 97 በኋላ ሁኔታዎች ፍጹም መቀየራቸውንና የሰራዊቱ አመራር ይበልጥ በሕወሃት ታጋዮች ቁጥጥር ስር የወደቀበት መሆኑን ያስታውሳሉ።

በምርጫ 97 ማግስት የአየር ሃይል አዛዥ ሜጀር ጄኔራል አለምሸት ደግፌን ጨምሮ አምስት የኦሮሞና የአማራ ጄኔራሎች ከሰራዊቱ ሲሰናበቱ በርካታ ከፍተኛ መኮንኖችም በተመሳሳይ ተባረዋል።

በ2003 ጄኔራል ተፈራ ማሞ በመንግስት ግልበጣ ተጠርጥረዋል ተብለው ሲታሰሩ ሌተናል ጄኔራል ባጫ ደበሌና ሌተናል ጄኔራል አበባው ታደሰ ደግሞ በጡረታ ተሸኝተዋል።

እነዚህ በጡረታ የተሸኙት ጄኔራሎች በሰራዊቱ ውስጥ ካሉት የሕወሃት ጄኔራሎች ጋር ሲነጻጸሩ ከብዙዎቹ በእድሜ ያነሱ መሆናቸውም ታውቋል።