በመስቀል ዓደባባይ የቦንብ ፍንዳታ የተጠረጠሩት የብሄራዊ መረጃና ደህንነት መምሪያ ኃላፊ ተስፋዬ ኡርጌን ጨምሮ በሌሎች ተጠርጣሪዎች ላይ የምርመራ ቀጠሮው ተራዘመ

በመስቀል ዓደባባይ የቦንብ ፍንዳታ የተጠረጠሩት የብሄራዊ መረጃና ደህንነት መምሪያ ኃላፊ ተስፋዬ ኡርጌን ጨምሮ በሌሎች ተጠርጣሪዎች ላይ የምርመራ ቀጠሮው ተራዘመ
( ኢሳት ዜና ነሐሴ 02 ቀን 2010 ዓ/ም ) ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ በአጭር ጊዜ ውስጥ ላስመዘገቡት የለውጥ ጅምሮችን በመደገፍ ሰኔ 16 ቀን 2010 ዓ.ም የምስጋና እና የድጋፍ ሰልፍ ላይ የቦንብ ጥቃት መፈፀሙ ይታወሳል። በወቅቱ የደረሰውን ጥቃት አቀናብረዋል፣ ሃላፊነታቸውን በአግባቡ አልተወጡም ተብለው ተጠርጥረው የተያዙት የብሄራዊ መረጃና ደህንነት መምሪያ አዛዥ ተስፋዬ ኡርጌ ላይ ፍርድ ቤቱ ተጨማሪ የምርመራ ጊዜ ተሰጠ።
መርማሪ ፖሊስ የምስክር ቃል መቀበሉን፣ የገንዘብ ድጋፍ መደረጉ ላይ ከፋይናንስ ተቋም ምላሽ ማመጣቱን፣ በቦንቡ ጉዳት የደረሰባቸው ግለሰቦች የጉዳት መጠንን እና የሟቾችን አስከሬን ምርመራ ወጤት የሚገለጽ የህክምና ማስረጃን ጨምሮ የቦንቡ የቴክኒክ ውጤትን ማምጣቱን፣ የድምጽ ቅጂን በተመለከተ ከኢትዮ-ቴሌኮም ማስረጃ ማመጣቱን ተሳትፎ አላቸው የተባሉ ሌሎች በአገር ውስጥና በውጪ የሚኖሩ የሽብር ቡድን አካላትን መያዢያ ከፍርድ ቤት ማውጣቱን ለችሎቱ ገልጿል።
ተጨማሪ ቀሩኝ ያላቸውን ከአገር ውጪ የሚገኙ ተጠርጣሪዎችን ለመያዝ ከአገራቱ ጋር በመነጋገር ላይ መሆኑንም ጠቅሷል። ተጠርጣሪዎቹን በቁጥጥር ስር ለማዋል ተስፋዬ ኡርጌ በርካታ ያፈሩት ሃብትን ምንጭ ለማጣራት እንዲቻል፤ ከተቋማቸው በተጨማሪ የሰነድ ማስረጃ ለመስበሰብና ሌሎች ቀሪ ምርመራዎችን ለማከናወን ተጨማሪ የ14 ቀናት የጊዜ ቀጠሮ ይሰጠኝ ሲል ጠይቋል።
የተጠርጣሪ ተከሳሽ ተስፋዬ ኡርጌ ጠበቃ በበኩላቸው “ደንበኛዬ ከተቋሙ ሰነድ ማውጣት አይችሉም። በዋስ ተለቀው ምርመራው መቀጠል ይችላል።” ሲሉ የመርማሪ ፖሊስ ተጨማሪ የምርመራ ጊዜ እዲራዘምለት መጠየቁን ተቃውመዋል።
ፍርድቤቱ በበኩሉ “ተጠርጣሪው በዋስ ቢወጡ የሚያደረሱት ተጽዕኖ ምንድነው?” ማለት ላቀረበው ጥያቄ፤ “ምስክሮች ከተጠርጣሪው ጋር ግንኙነት ሊኖራቸው ስለሚችል ምስክሮቻችንን ሊያሸሹበን ይችላሉ። ከተቋማቸው ማስረጃ ስናመጣ የሰነድ ማስረጃው ያለው ከስራቸው ባሉ ሰራተኞች በመሆኑ የሰነድ ማስረጃው ሊጠፋ ይችላል። በሃብት ምንጫቸው ለምናደረገው ማጣራት እንቅፋት ሊፈጥሩ ይችላሉ። በመሆኑ በዋስ ሊወጡ አይገባም።” ሲል ዋስትናውን በመቃወም ፖሊስ የመላከያ ምሽላ ተሰጥቷል።
ፍርድ ቤቱም የዋስትና ጥያቄውን ውድቅ በማድረግ ለመርማሪ ፖሊስ ተጨማሪ የሰባት ቀናት የምርመራ ጊዜ ፈቅዷል።
ተጨማሪም በተመሳሳይ ክስ በተከሰሱት በየነ ቡላና አብዲሳ መገርሳ ላይ መርማሪ ፖሊስ ያደረገውን ምርመራ አጣቶ የምርመራ መዝገቡን አጠናቆ ለአቃቤ ህግ አስረክቧል።
ጠቅላይ አቃቢ ህግ በበኩሉ መዝገቡን ሐምሌ 27 ቀን 2010 ዓ.ም መረከቡን አስታውቋል። የመርመራ መዝገቡ በምስልና በድምጽ የታገዘና በርካታ ውስብስብ የወንጀል አፈጻጸም የያዘ በመሆኑ መዝገቡን አይቶ የተናጠል ወንጀል ደርጊታቸውን በግልጽ ለፍርድ ቤቱ ለማቀረብ እና ክስ ለመመስረት የ15 ቀናት የጊዜ ቀጠሮ እንዲሰጠው ፍረድቤቱን ጠይቋል።
ተጠርጣሪ በየነ ቡላ “ከተያዝኩ አንድ ወር ሞላኝ። ቤተሰቤ የተበተነ ሲሆን የዛሬ 10 ቀን ነው ቃሌን ፖሊስ የወሰደው። በዚህ 10 ቀን ክስ ሊመሰረት ይችል ነበር። ፍትህ ሊጓተት አይገባም። የዋስትና መብቴ ተከብሮ ወጥቼ ጉዳዬን ለከታተል ይፈቀድልኝ።” በማለት ተጨማሪ ጊዜ ቀጠሮውን በመቃወም የዋስትና መብቱ እንዲከበርለት ጠይቋል።
ሌላው ተጠርጣሪ አብዲሳ መገርሳ በጠበቃቸው አማካኝነት ዋስትና መብታውቸ እንዲፈቀድላቸው ጠይቀዋል።
ጉዳዩ ውስብስብ ወንጀል እንደመሆኑ የሌሎች ተጠርጣረዎች መዝገብ ያለ በመሆኑ በዋስ ቢወጡ ምስክር ሊያሸሹብኝ ስለሚችሉ ዋስትናውን እቃወማለው ሲል አቃቤ ህግ ዋስትናውን ተቃውሞ አቅርቧል።
ፍርድ ቤቱ የተጠርጣሪዎችን ዋስትና ጥያቄ አልተቀበለውም። ለአቃቤ ህግ ተጨማሪ የምርመራ ጊዜ የ10 ቀን ጊዜ ፈቅዷል።