በሊቢያ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን ወደ ማይታወቁ ስፍራዎች እየተወሰዱ ነው

ሚያዚያ ፳፰ (ሃያ ስምንት) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም

ኢሳት ዜና:-በተለያዩ እስር ቤቶች የሚገኙ ኢትዮጵያውያኖች እንደገለጹት ከተለያዩ እስር ቤቶች የተውጣጡ በርካታ ኢትዮጵያውያን ወደ አልታወቁ ስፍራዎች ተሰደዋል።

የኢትዮጵያ ዜጎች ከሁሉም ዜጎች ባነሰ ሁኔታ እንደሚስተናገዱ የሚገልጹት እስረኞች ሴቶች ይደፈራሉ፣ ወንዶች ገንዘብ ካላመጡ ይደበደባሉ።

ኩሚስ በሚባል እስር ቤት ውስጥ ላለፉት 9 ወራት ታስሮ በስቃይ ላይ የሚገኘው ሽሬ እንደ ስላሴ ተወልዶ ያደገው መምህር ሙሴ ዘ ሚካኤል  በዛሬው እለት ብቻ 17 ኢትዮጵያውያን እያለቀሱ ወደ አልታወቀ ስፍራ መወሰዳቸውን ተናግሯል።

የኢትዮጵያ መንግስት ምንም እንዳላደረገላቸው የገለጸው ሙሴ ዘ ሚካኤል  ፣ በሊቢያ ብቻ ከ7 ሺ ያላነሱ ኢትዮጵያውያኖች በእስር ላይ እንደሚገኙ ገልጿል  በሊቢያ ኢትዮጵያዊ ሆኖ መገኘት ሞትን መጋበዝ መሆኑን መምህር ሙሴ አክሎ ተናግሯል።

በጉዳዩ ዙሪያ የኢትዮጵያን መንግስት አስተያየት ለማግኘት ያደረግነው ሙከራ አልተሳካም።