ሼክ ሙሃመድ አላሙዲን ከባለስልጣናት ጋር ባላቸው ቀረቤታ የህዝብ ሃብት የሆኑ ኩባንያዎችን ወደ ግል እንዲያዞሩ ረድቷቸዋል ተባለ

ጥር ፳(ሃያ) ቀን ፳፻፯ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-የፕራይቬታይዜሽንና የመንግስት ልማት ድርጅቶች ተቆጣጣሪ ኤጀንሲ የመንግስት ልማት ድርጅቶችን መሸጥ ከጀመረበት ከ1997 ዓ.ም እስከ 2006 ዓ.ም ድረስ ባሉት ጊዜያት ከሸጣቸው 370 ድርጅቶች መካከል ሼህ አልአሙዲ ወደ 30 የሚጠጉትንና እጅግ አትራፊ የሆኑ ድርጅቶችን በርካሽ ዋጋ መሰብሰብ መቻላቸው ስርአቱ ለተዘፈቀበት ሙስና ማሳያ መሆኑን ጉዳዩን በቅርብ የሚከታተሉ ወገኖች ገልጸዋል።

ሼሁ የለገደንቢን ወርቅ ማዕድን በአሁኑ ወቅት ሚድሮክ ወርቅ ማዕድን ኩባንያ እየተባለ የሚታወቀውን  በ1989 ዓ.ም በብር 1 ቢሊዮን 128 ሚሊዮን 543 ሺ ከ28  ሳንቲም  በመግዛት በእጃቸው አስገብተዋል፡፡ ኩባንያው በ2006 በጀት ዓመት ብቻ ከ100 ሚሊየን ዶላር በላይ የውጭ ምንዛሪ በማስገባቱ ምክንያት ባለፈው ወር የኢትዮጽያ ንግድ ባንክ ሸልሞታል፡፡ ለኢህአዴግ ከፍተኛ ጥቂት አመራሮች ባላቸው ቅርበት የሚታወቁት ሼህ አልአሙዲ ባለፉት 17 ዓመታት

በፕራይቬታይዜሽን ስም በይስሙላ በሚወጡ ጨረታዎች ወሳኝ የሆኑ ኢንዱስትሪዎችንና የእርሻ ድርጅቶችን በርካሽ ዋጋ በእጃቸው ማስገባት እንደቻሉ መረጃዎችን ዋቢ በማድረግ ምንጮች ገልጸዋል፡፡ ከነዚህ ድርጅቶች መካከል በቀድሞ ስማቸው የሚታወቁትን ፔፕሲ ኮላ ፋብሪካዎች፣ ድል ቀለም ፋብሪካ ፣ዋንዛ የእንጨት ውጤቶች ድርጅት፣ ዪኒቨርሳል እና አዋሽ ቆዳ ሁለት ፋብሪካዎች፣ ጎንደር፣ ድሬዳዋ እና ኮምቦልቻ ሶስት የሥጋ ውጤቶች ፋብሪካዎች፣ ለገደንቢ ወርቅ ፋብሪካ፣ አዲስ ጎማ (ሆራይዘን) ፋብሪካ፣ ደብረዘይት ሆራ ራስሆቴል፣ ውሽውሽ ጉመሮ ሻይ ልማትና ገበያ ድርጅት ፣ጎጃም፣ጎንደር፣የላይኛውና የታችኛው  ብር ሸለቆ እርሻ ልማት፣ጎጀብ እርሻ ልማት፣ ጥቁር አባይ ጫማ ፋብሪካ እና የመሳሰሉት ይጠቀሳሉ፡፡

ሼህ አላሙዲን በተለይ ደብረዘይት ሆራ ራስ ሆቴልን እጅግ ርካሽ በሚባል በ9 ሚሊየን ብር በ1990 ዓ.ም ቢገዙም እስከአሁን ምክንያቱ ባልታወቀ ሁኔታ አጥረው ከማስቀመጥ ውጪ ሊሰሩበት አልቻሉም፡፡

ሼህ አልአሙዲን በተለይ እንደእነአቶ በረከት ስምኦን የመሳሰሉ ከፍተኛ የመንግስት ባለስልጣናት ጋር በመቀራረብ የግልና የቤተሰቦቻቸውን የህክምናና መዝናኛ እንዲሁም አንዳንድ ወጪዎችን በመሸፈን፣ እንደቤትና መኪና የመሳሰሉ ውድ ስጦታዎችን በመስጠት ግልጽ የሆነ ሙስና እንደሚፈጽሙ፣ለዚህ ወሮታቸውም የጠየቁትን  የህዝብ ሐብት ያለአንዳች ችግር እንዲወስዱ እንደሚደረግ ምንቾች ገልጸዋል። ሼክ አላሙዲ ከ10 አመት በፊት ኢህአዴግን በመደገፍ በምርጫ ቅስቀሳ መሳተፋቸው ይታወቃል።