”የቀድሞውጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ ፎቶዎችና ፖስተሮች ይነሱ! ” ሲል ሪፖርተር ጋዜጣ ጠየቀ

ጥር ፳፱ (ሀያ ዘጠኝ) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም

ኢሳት ዜና:-ጋዜጣው በዛሬው ርዕሰ-አንቀጹ የ አቶ መለስ ፎቶና ፖስተር ያልተሰቀለበትን የ አዲስ አበባ ጎዳና ፈልጎ ማግኘት እንደማይቻልና ፎቷቸው በሁሉም ስፍራ እንዳለ በመጥቀስ፦<<አሁን ግን ይብቃ! ፎቶዎቹና ፖስተሮቹ ይነሱ!እንላለን>> ሰል በአጽንኦት ጠይቋል።

ፖስተሮቹ ሊያስተላልፉ የሚገባቸውን መልእክት በክብር እንደተሰቀሉ በክብር ይነሱ ያለው ጋዜጣው፤ ዝናምና ፀሀይ እስኪያበላሻቸው ዝም ብሎ መጠበቅ  ማቆሸሽና ትርጉም ማሳጣት ነው ብሏል።

ፖስተሮቹ ዘላለማዊ ተደርገው መወሰድ እንደሌለባቸውም ጋዜጣው አቋሙን ገልጿል።

በማያያዝም፦<<በፖስተሮቹና በፎቶግራፎቹ መሰቀል ለመነገድ፣ ለማስመሰልና ለማጭበርበር የሚፈልግ ሰው ካለም በቃህ ሊባል ይገባል፡፡ በጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ ስም አትነግድ፣ አታጭበርብር፣ አታታል ሊባል ይገባዋል፡፡>>ብሏል።

ከዚህም ሌላ በቅርቡ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የ አቶ መለስ ፋውንዴሽን እንዲቋቋም መወሰኑን ያወሳው ጋዜጣው፤ ፋውንዴሽኑን  ለምን ተቋቋመ? የሚል ተቃውሞ ባይኖረውም ፤የመቋቋሙ ጉዳይ በፓርላማ መታወጅ እንደማይጠበቅበት አስፍሯል።

እንደ ጋዜጣው ርዕሰ-አንቀጽ ፋውንዴሽኑ በቤተሰብ፣በወዳጆች፣በደጋፊዎችና በፖለቲካ ፓርቲዎች በህግ ሳይሆን በፈቃደኝነትና በፍላጎት ሊቋቋም ይችል ነበር።

አስከትሎም፦<<በተግባር የማይደገፍ የፎቶና የፖስተር መለጣጠፍ መንፈስ ግን ተቀባይነት ሊኖረው አይገባም፡፡ ሒደቱም በጊዜ ወሰን ውስጥ ሊከናወን ይገባል፡፡ በመሆኑም የዚህ ዓይነቱን ጨዋታ አቁመን ተግባር ላይ እናተኩር፡፡ ፖስተሮቹ ይነሱ፡፡ ፎቶዎች ይነሱ፡፡ እየተቀዳደዱና እየቆሸሹ ናቸው፡፡>>ብሏል።

ቃላትም ትርጉም ይኑራቸው፡፡ በቃላት ድርደራ ብቻ ‹‹ራዕይ›› እና ‹‹ሌጋሲ›› እያልን እየለፈለፍን በተግባር ግን ራዕዩንና ሌጋሲውን የሚፃረር ሥራ የምንሠራ ከሆነ ያስተዛዝባል>>ያለው ሪፖርተር፤ << የእሳቸውን ስምና ሥራ መነገጃና መደለያ የምናደርገው ከሆነ ከሞራል አንፃር ያስወቅሰናል ብቻ ሳይሆን በታሪክም እንጠየቅበታለን>>ብሏል።

ከርእሰ አንቀጹ ስር በርካታ አንባብያን አስተያየታቸውን ሰጥተዋል።

መለስ 123 የተባለ አስተያዬት ሰጪ፦<<ሁሉም ሰው ፎቶውን ማዬት ሰልችቷል፤አንገሽግሾታል ወደዚያ አንሱልን>>ሲል፤ቶማስ ቶማስ የተባለ ደግሞ፦<<እኔን የናፈቀኝ ቀጥሎ ደግሞ የማን እንደሚሰቀል ማወቅ ነው>>ብሏል።

ጀፒዲዲ የተባለ አስተያዬት ሰዐጪ ደግሞ፦<<ስለመለስ ዜናዊ መስማቱና ማየቱ የኢትዮጵያን ሕዝብ አንገሽግሾታል እጅ እጅ ብሎታል ሀገር ጥሎ ቢጥፋ ደስ ይለዋል ፎቶዎቹን የሚቀዳድድባቸው ጊዜ እየናፈቀ ነው >>ብሏል።

ኢትዮጵዮፍርደም ደግሞ ” በለውጡ ጊዜ የምንቀደው እንዳናጣ ይቀመጡ ብሎአል። የፖስተሩን መቀመጥ የደገፉ አንዳንድ አስተያየት ሰጪዎችም ሀሰባቸውን አስፍረዋል።

ኢሳት በባንቢስ አካባቢ ያሉት የመለስ ፎቶዎች እንዲወርዱ መደረጋቸውን ከወር በፊት መዘገቡ ይታወሳል። ሪፖርተር በይፋ ፎቶዎቹ ይነሱ የሚል ቅስቀሳ የጀመረው የኢህአዴግ መሪዎችን ከጎኑ አሰልፎ ከሆ እቅዱ ተግባራዊ ሊሆን ይችላል፣ ጋዜጣው በራሱ ተነሳሽነት ያሰፈረው ሀሳብ ከሆነ ግን ጋዜጣውን ከኢህአዴግ ጋር የሚያላትመው ይሆናል፣ ምክንያቱም ኢህአዴግ ለፖስተሮቹ ማሰሪያ በሚሊዮን የሚቆጠር ገንዘብ አፍስሶባቸዋልና ሲል አንድ አስተያየት ሰጪ ተናግሯል።

ይህ በእንዲህ እንዳለ የመለስን ህይወት ታሪክ የያዘውን አዲስ ራእይ መጽሄት የኢህአዴግ አባል የሆኑት በመላ በ100 ብር ሁለት ሁለት ቅጅ እንዲገዙ በመታዘዛቸው አባላቱ ቅሬታቸውን እያቀረቡ ነው። አባላቱ ለኢሳት እንደተናገሩት መጽሄቱ የታሰበውን ያክል ሊሸጥ ባለመቻሉ እያንዳንዱ አባል እንዲገዛ ግዴታ ተጥሎበታል።