ሰማያዊ ፓርቲ እስከ አሁን ፈቃድ አላገኘም

ሚያዚያ ፲፭ (አስራ አምስት) ቀን ፳፻፬ ዓ/ም

ኢሳት ዜና:-በወጣቶችና በምሁራን የተገነባው አዲሱ ሰማያዊ ፓርቲ እስከ ዛሬ ፈቃድ ሊያገኝ አልቻለም። ከምርጫ ቦርድ ያገኘነው መረጃ እንደሚያመለክተው የፓርቲው መስራቾች በቦርዱ የታዘዙትን መስፈርቶች ሁሉ ቢያሙዋሉም፣ የቦርዱ አባላት ግን ፈቃዱን ሊሰጡዋቸው አልቻሉም።

አንድ ስማቸው እንዳይጠቀስ የፈለጉ የድርጅቱ ሰራተኛ ለኢሳት እንዳሉት፣ ፓርቲው በመላ አገሪቱ በብዙ ሺ የሚቆጠሩ ፊርማዎችን አሰባስቦ ለህዝብ ይፋ ማድረጉ ቢረጋገጥም፣ የቦርድ አባላት ግን ከመንግስት አቅጣጫ አልመጣልንም የሚል ምክንያት በማቅረብ ፣ ፈቃዱን ሊሰጡዋቸው አልቻሉም። የመንግስት አቅጣጫ የሚባለው ፣ ከኢህአዴግ ጽህፈት ቤት የሚሰጠው ይሁንታ መሆኑን ለማወቅ ተችሎአል።

ይህ በእንዲህ እንዳለ ታዋቂ ምሁራን ለፓርቲው አባላት ትምህርቶችን እየሰጡ ነው። በቅርቡ ረዳት ፕሬፌሰር ዝናቡ አበራ በኢትዮጵያ ውስጥ በየ14 አመቱ የልውጥ እንቅስቃሴ እንደሚኖር ለፓርቲው አባላት ትምህርት ሰጥዋል። በሚቀጥለው ሳምንት ደግሞ ኢኮኖሚስቱ ዶ/ር በፈቃዱ ደገፌ ለወጣቶች ትምህርት እንደሚሰጡ ለማወቅ ተችሎአል።

የሰማያዊ ፓርቲ አመራሮችን ፈቃድ በመከልከላቸው ዙሪያ ለማነጋገር ሙከራ ብናደርግም አልተሳካልንም።

___________________________________________________________________________________________________________________________________________________

ESAT is the first independent Ethiopian satellite service tasked to produce accurate and balanced news and information, as well as other entertainment, sports and cultural programming created for and by Ethiopians.

ESAT is committed to the highest standards of broadcast journalism and programming and will strive to provide an outlet of expression to all segments of the diverse Ethiopian community worldwide