መከላከያ ሰራዊቱ በርካታ የጋምቤላ ነዋሪዎችን ገደለ

ሚያዚያ ፳፭ (ሃያ አምስት) ቀን ፳፻፬ ዓ/ም

ኢሳት ዜና:-የኢትዮጵያ መከላከያ ሰራዊት በጋምቤላ ክልል በፖከዲ መንደር ውስጥ 5 ሰዎችን መግደሉን የደረሰን ዜና ያመለክታል። ከማቾቹ ውስጥ አንድ መምህር፣ ሁለት ተማሪዎችና አንድ አርሶ አደር ይገኙበታል። የአይን ምስክሮች እንዳሉት በርካታ ተማሪዎች ተኩስ በተከፈተበት ወቅት ወደ ጫካ ገብተው የሸሹ በመሆናቸው የሟቾች ቁጥር ሳይጨምር አይቀርም። በጥቃቱ የቆሰሉትም በርካታ መሆናቸው ተገልጿል።

በኮጎ ወረዳ ጋሀሪ በሚባል መንደር ደግሞ 4 ገበሬዎች ተገድለዋል። በአኮቦ ወረዳም እንዲሁ ወታደሮቹ የደቡብ ሱዳንን ድንበር ተሻግረው በጋምቤላ ተወላጆች ላይ ጥቃት መፈጸማቸው ታውቋል።

ይህ በእንዲህ እንዳለ በዛሬው እለት የጋምቤላ ህዝብ ሰሞኑን በሼክ ሙሀመድ ሁሴን አላሙዲ ንብረት በሆነው በሳውዲ ስታር ኩባንያ ውስጥ ተቀጥረው ይሰሩ በነበሩ ኢትዮጵያውያን እና ፓኪስታናዊያን ላይ የደረሰውን ጥቃት እንዲያወግዙ የተጠሩ የከተማዋ ነዋሪዎች አስገራሚ ትእይንቶችን አሳይተዋል።

በሰልፉ ላይ የከተማው ነዋሪና የመንግስት ባለስልጣናት ይዘውት የወጡት መፈክር መለያየት፣ እንዲሁም ህዝቡ ንግግር ወደ ሚያደርጉት ወደ ክልሉ ፕሬዚዳንት ወደሆኑት አቶ ኦሞድ ኦቦንግ መጠጋት መጀመር ሰልፉ በ15 ደቂቃ ውስጥ እንዲበተን መደረጉን በስፍራው ተገኝቶ የተመለከተው ዘጋቢያችን  ኡጁሉ ኦሞት ገልጧል።

አንድ ማንነቱ ያልታወቀ ሰው ” መለስ ዜናዊ በጋምቤላ ዙሪያ ምነው ቀበቶህን ፈታህ? ” የሚል መፈክር ይዞ የታየ ሲሆን፣ የመንግስት ባለስልጣናት ደጋፊዎች ደግሞ ልማታችን እና የሰፈራ ፕሮግራም በአሸባሪዎች ሊደናቀፍ አይችልም የሚል መፈክር ይዘው ታይተዋል።

ሰልፈኛው በስታዲየም እንዲሰባሰብ ከተደረገ በሁዋላ በመንግስት ባለስልጣናት የቀረቡትን መፈክሮች አብሮ እንዲያሰማ በሚጠየቅበት ጊዜ በተቃራኒው የራሱን መፈክሮች ማሰማት መጀመሩን ዘገባው ያመለክታል። ከደቂቃዎች በሁዋላም ሰልፈኛው “ጥያቄዎች አሉን ፕሬዚዳንቱን መጠየቅ እንፈልጋለን” ማለት ሲጀምር ፣ ባለስልጣናቱ ጥያቄ ለመቀበል ፈቃደኛ አለመሆናቸውን፣ የዛሬው ሰልፍ አላማ  መፈክሮችን ለማሰማት መሆኑን በመናገር ጥያቄዎችን ለመቀበል ፈቃደኞች ሳይሆኑ ቀርተዋል።  ሰልፈኛው ወደ ፕሬዚዳንቱ መጠጋት ሲጀመር ብጥብጥ ሊነሳ ይችላል በሚል ስጋት ዝግጅቱ አልቋል እናመሰግናለን በማለት ፕሬዚዳንቱን ይዘው ሄደዋል።

የመንግስት ሰራተኞች በግዴታ ወደ ሰልፉ እንዲወጡ የተደረገ ሲሆን፣ መፈክሮችም ተዘጋጅተው ነበር የቀረቡላቸው። ከፍተኛ ውጥረት በታየበት በዚህ ሰልፍ የከተማው ነዋሪዎች የሆኑ  የአኝዋክ ተወላጆች አለመገኘታቸው ታውቋል።

በጋምቤላ በዛሬው እለት ሰላማዊ ሰልፍ እንደሚካሄድ ታማኝ ምንጮችን በመጥቀስ ዘግቦ እንደነበር ይታወሳል።

በሌላ ዜና ደግሞ በቀርቡ በሳውዲ ስታር ሰራተኞች ላይ በደረሰው ጥቃት ቆስለው በመቱ ሆስፒታል በህክምና ሲረዱ ከቆዩት ኢትዮጵያውያን መካከል አንደኛው ህይወቱ ማለፉ ተውቋል።

___________________________________________________________________________________________________________________________________________________

ESAT is the first independent Ethiopian satellite service tasked to produce accurate and balanced news and information, as well as other entertainment, sports and cultural programming created for and by Ethiopians.

ESAT is committed to the highest standards of broadcast journalism and programming and will strive to provide an outlet of expression to all segments of the diverse Ethiopian community worldwide