መንግስት ሁኔታው በርዷል በማለት በውጭ ጉዳይ መስሪያ ቤት ቃል አቀባይ በኩል ቢናገርም፣ ኢሳት ያነጋገራቸው ኢትዮጵያውያን ግን ችግሩ መክፋቱን እየገለጹ ነው።

ህዳር (አራት)ቀን ፳፻፮ / ኢሳት ዜና :-በሴቶች ካምፕ ያለው ሁኔታ እጅግ አስከፊ መሆኑን ኢትዮጵያውያን ሴቶች ይነጋራሉ።

ቀን በጸሀይ ማታ ደግሞ በብርድ እንድናሳልፍ እየተገደድን ነው የምትለው ሌላዋ እስረኛ ሳሚራ፣ ህጻናት እና እናቶች በምግብ እጦት እየተጎዱ ለበሽታም እየተዳረጉ ነው ትላለች። ባለፉት አራት ቀናት የወለዱ እናቶች መኖራቸውን የምትገልጸው ሳሚራ፣ የሳውዲ ፖሊሶች ወላዶችን የት እንደወሰዱዋቸው እንደማታውቅ ገልጻለች። ሀብታም የተባለቸውም እንዲሁ እርሷ በምትገኝበት ቦታ ላይ በተለይ ህጻናት ቆሻሻ ውስጥ መጣላቸውን፣ የኢትዮጵያ መንግስት መፍትሄ ሊሰጣቸው እንደላቸለም ገልጻለች። ሌላዋ አስተያየት ሰጪ በበኩሉዋ የሳውዲ ወጣቶች ኢትዮጵያውያንን ኢላማ አድርገው በመንቀሳቀስ ላይ መሆናቸውን ተናግራለች።

በወንዶች እስር ቤት ውስጥ ከፍተኛው ችግር የምግብ እጥረት መሆኑን የሚናገሩት እስረኞች፣ ከቀኑ 10 ሰአትና ከሌሊቱ 7 ሰአት የሚሰጣቸውን አነስተኛ ምግብ ተሻምተው እየተመገቡ ነው። ኢትዮጵያዊያኑ እስካሁን ድረስ አንድም የኢትዮጵያ መንግስት ባለስልጣን መጥቶ እንዳላነጋገራቸው ተናግረው፣ መቼ ከአገሪቱ እንደሚወጡም መረጃ እንደሌላቸው ገልጸዋል።