መንግስታዊ ተቋማት በሕዝብ ላይ የሚያደርሱት አስተዳደራዊ በደሎች ከዓመት ዓመት እያደገ ነው

ሚያዚያ ፯ (ሰባት) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም

ኢሳት ዜና:- የሕዝብ እምባ ጠባቂ ተቋም ከሕዝብ ከሚቀርቡለት አስተዳደራዊ በደሎች መካከል በመንግስት ላይ በተለይ በፍትህ
ተቋማት ላይ የሚቀርበው የአስተዳደራዊ ቅሬታ ብዛት ከፍተኛ መሆኑን አንድ ጥናት አመለከተ፡፡
ላለፉት አምስት ዓመታት ወደተቋሙ የመጡ ቅሬታዎች መካከል አንድ ሶስተኛ ወይም 31 በመቶ ያህል ከፍተኛ ድርሻ
የያዙት የመንግስት ተቋማት ላይ የሚቀርቡ ቅሬታዎች ማለትም ከቀበሌ መዋቅር አንስቶ አስከ ፌዴራል ባሉ እርከኖች
የሚመለከቱ ሲሆኑ ከነዚህ ተቋማት መካከል የፍትህ ዘርፍ ላይ የሚቀርቡት አቤቱታዎች በመጀመሪያው ረድፍ ላይ
እንደሚገኙ ጥናቱ ይጠቁማል፡፡

ጥናቱ አቤቱታዎቹ በየዓመቱ በአማካይ በሴክተር መ/ቤቶች በ160 በመቶ እያደጉ ናቸው ያለ ሲሆን
ከፍትሕ ተቋማት ጋር በተያያዘ የሚቀርቡት አቤቱታዎች ብዛት በ138 በመቶ ዕድገት ማሳየቱን
ጠቁሟል፡፡

ለትምህርት ሚኒስቴር እና ለሌሎች የመንግስት ተቋማት የሚቀርቡ አቤቱታዎች ብዛት በ221 በመቶ፣ከመሬት
አስተዳደር መስሪያ ቤቶች ጋር በተያያዘ የሚቀርቡ አቤቱታዎች ብዛት በየዓመቱ በአማካይ በ409 በመቶ ከፍተኛ
ዕድገት እያሳዩ መምጣታቸውን ጥናቱ ይጠቁማል፡፡
ከክልሎች ጋር ሲነጻጸር በአዲስአበባ አቤቱታ አቅራቢ ቁጥር ከፍተኛ መሆኑን ጥናቱ ያመለክታል፡፡“ ከአገሪቱ ሕዝብ ብዛት አምስት በመቶ የማይደርሰውን የሕዝብ ብዛት የያዘችው አዲስአበባ ለተቋሙ ከሚቀርቡ የአስተዳደር በደል አቤቱታዎች አስከ 60 በመቶ ያህሉን ትሽፍናለች፡፡ ይህ የሆነበት ምክንያት የተቋሙ አገልግሎቶች በከተሞች አካባቢ ብቻ በመወሰኑ ነው ብሏል፡፡

ከሕዝብ እምባ ጠባቂ ተቋም የተገኘው ይህው ጥናት ለአቤቱታዎቹ በየኣመቱ መጨመር ምክንያት ናቸው ያላቸውን ጉዳዮች
ዘርዝሯል፡፡

ለሕዝቡ አቤቱታ መጨመር አንዱና ዋንኛው ምክንያት የህዝብ እምባ ጠባቂ ተቋም እንደነዚህ ዓይነት
ጉዳዮችን እንደሚመለከት በሕዝብ ዘንድ ግንዛቤ አለመኖሩና ተቋሙ መኖሩን የተገነዘቡ ሰዎች በየዓመቱ በመጨመራቸው
መሆኑን ይጠቅሳል፡፡

ጥናቱ ይህን ይበል እንጂ የእምባ ጠባቂ ተቋም ምንጮቻችን እንዳሉት አቤቱታዎቹ እየጨመሩ የመጡት በአገሪትዋ የመልካም አስተዳደር ችግሮች በየጊዜው መባባስ ምክንያት አስተዳደራዊ በደሎች ከመብዛታቸው ጋር በተያያዘ መሆኑን በመጥቀስ የጥናቱን ግኝት የመንግስትን ገመና ለመሸፈን የተቀመጠ ነው ሲሉ ያጣጥሉታል፡፡

በአዋጅ ቁጥር 211/1992 የተቋቋመው የህዝብ እምባ ጠባቂ ተቋም ዋንኛ ተግባሩ ሕዝቡ ለሚያጋጥመውን
አስተዳደራዊ በደሎች ቅሬታ ሲቀርብለት ተከታትሎ እርማት እንዲያገኝ በማድረግ የዜጎች መብትና ጥቅሞች በአስፈጻሚው
አካል መከበራቸውን ማረጋገጥ ቢሆንም፣  ተቋሙ አቤቱታዎችን መቅረፍ ባለመቻሉ “ጥርስ የሌለው አንበሳ፣የህዝብ እምባ
አባባሽ ተቋም” የሚሉ ቅጽል ስሞችን አትርፏል፡፡