መምህራን ለአዲሱ መንግስት የታዛዥነት ቃል ኪዳናቸውን እንዲያድሱ የሚያደርግ ጉባኤ ተዘጋጀ

መስከረም ፳፪ (ሃያ ሁለት) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም

ኢሳት ዜና:-መንግስት ተሀድሶ በማለት በሚጠራው በዚህ የቃል ኪዳን ማደሻ ጉባኤ ላይ መምህራን የአቶ መለስ ዜናዊን ራእይ ለማስቀጠል ቃል  እንዲገቡ ይጠየቃሉ ።

በንፋስ ስልክ ላፍቶ ክፍለ ከተማ በቁጥር ን/ስ/ላ/ወ1/0342/2005 በቀን 10/01/2005ዓም ድጋፍ እንዲደረግ ስለመጠየቅ በሚል ርእስ የተጻፈው ደብዳቤ እንደሚያሳየው ትምህርት ቤቶች ለዚሁ ለተሀድሶ ስራ ማስፈጸሚያ እስከ 600 መቶ ሺ ብር የሚጠጋ ገንዘብ እንዲያዋጡ ተጠይቀዋል ።

ደብዳቤው የተሀድሶውን አስፈላጊነት  ሲገልጽ ” መምህራንና ሰራተኞችን ተሀድሶ ፕሮግራም በማድረግ እውቅና ለመስጠትና የተጀመረውን የልማትና የመልካም አስተዳደር ተግባር በትምህርት ቤቶች ለማስፈንና ጅምሮችን ወደ ላቀ ደረጃ ለማሸጋገር ቃል ኪዳን የምንገባበት ነው” ብሎአል።

ምክትል ጠ/ሚኒስትሩና የትምህርት ሚኒስትሩ አቶ ደመቀ መኮንን ትናንት በተከፈተው የትምህርት ጉባኤ ላይ ” በቅርቡ ያጣናቸው ጠቅላይ ሚኒስቴር መለስ ዜናዊ ለመጪው ትውልድ እውቀትን እንጂ ድንቁርና አናወርስም የድሕነትን ተራራ ለመናድ ቁልፍ መሳሪያው ትምህርት ነው፣ ልማት ማለት የሰው ሃብት ልማት ነው ይህ ደግሞ ያለትምህርት አይታሰብ በሚል መርሐቸው ባስቀመጦዋቸው እቅዶች ሰፊ ሰራዎች ተሰርተዋል” ብለዋል።

የኢህአዴግ መንግስት ለመምህራን በሚያዘጋጃቸው የተሀድሶ ዝግጅቶ ላይ፣ መምህራኑ የድርጅት አባልነት ፎርም እንዲሞሉ ያስገድዳል፣ የተሀዶሶ ዝግጅቱ የፖለቲካ ስልጠና መስጪ ነው በማለት መምህራን እንደሚተቹ ይታወቃል።

___________________________________________________________________________________________________________________________________________________________________________

ESAT is the first independent Ethiopian satellite service tasked to produce accurate and balanced news and information, as well as other entertainment, sports and cultural programming created for and by Ethiopians.

ESAT is committed to the highest standards of broadcast journalism and programming and will strive to provide an outlet of expression to all segments of the diverse Ethiopian community worldwide