ሒዝቦላህ ከቢሊየነሮች ዝርዝር ውስጥ ስሙ ሰፈረ

(ኢሳት ዲሲ–ሚያዚያ 2/2010)በአለም ከሚገኙ አሸባሪ ቡድኖች በሃብት ግንባር ቀደም የሆነውና ከቢሊየነሮች ዝርዝር ውስጥ ስሙ የሰፈረው ሒዝቦላህ መሆኑ ታወቀ።

በኢኮኖሚና በፋይናንስ ጉዳዮች ላይ ዘገባ የሚያቀርበውና የቢሊየነሮችን ዝርዝር ይፋ የሚያደርገው ፎርብስ እንደዘገበው ሒዝቦላህ ጠቅላላ አመታዊ ገቢው 1 ነጥብ 1 ቢሊየን የአሜሪካን ዶላር ደርሷል።

65 ሺ ያህል ተዋጊዎች እንዳሉት የሚታመነውና በተለይ በምዕራባውያን ዘንድ በአሸባሪነት የተፈረጀው ሒዝቦላህ በኢራን መንግስት በአመት 200ሺ ዶላር ያህል ድጋፍ ሲደረግለት መቆየቱ ተመልክቷል።

ይህ ድጋፍ በአሁኑ ወቅት በአመት ወደ 800 ሺ ዶላር ማደጉን የገለጸው ፎርብስ ከተለያዩ ምንጮች ሒዝቦላህ በአመት የሚያገኘው ገንዘብ 1 ነጥብ 1 ቢሊየን ዶላር መድረሱን አመልክቷል።

በምዕራባዉያኑ በአሸባሪነት የተፈረጀው ሒዝቦላህ በሊባኖስ ውስጥ ሕጋዊ ሆኖ የሚንቀሳቀስ ፓርቲ ነው።

ከሃገሪቱ 128 የፓርላማ ወንበር 12ቱን እንዲሁም ከ30 የካቢኔ ስፍራዎች ደግሞ ሁለቱን መቆጣጠሩ ታውቋል።

እንደ አውሮፓውያኑ አቆጣጠር በ1985 የተመሰረተውና መቀመጫውን በሊባኖስ ርዕሰ መዲና ቤይሩት ያደረገው ሒዝቦላህ እስላማዊ ብሔርተኝነትን የሚያቀነቅን ሲሆን ፣ጸረ-ጺዮናዊ እንዲሁም ጸረ-ምዕራብ ኢምፔሪያሊዝም እንደሆነም ተመልክቷል።

አሜሪካ፣እስራኤል፣ሳውዲአረቢያ፣ባህሬን፣ካናዳ፣አውስትራሊያ፣ፈረንሳይና ጃፓንን ጨምሮ ከ10 የሚበልጡ ሀገራት በአሸባሪነት የፈረጁት ሒዝቦላህ ከኢራን፣ሶሪያ፣ኢራቅ፣እንዲሁም ኩባ፣ሰሜን ኮሪያና ቬንዚዌላ ጋር ጥሩ ወዳጅነት እንዳለውም ታውቋል።