ላለፉት 2 አመታት ስርአቱን በሀይል ለመፈታተን ከሞከሩት ሁሉ የሀይማኖት እንቅስቃሴዎች ዋነኞቹ እንደነበሩ ኢህአዴግ አስታወቀ

ነሃሴ ፳፰(ሃያ ስምንት)ቀን ፳፻፭ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-ፓርቲው አዲስ ራእይ በሚባለው ልሳኑ ” ፣ በሀይማኖት ሽፋን የሚካሄዱ የፖለቲካ እንቅስቃሴዎች እየተዳከሙና እየተጋለጡ መሄዳቸው ባይቀርም ባለፉት ሁለት አመታት ልማታዊና ዲሞክራሲያዊ ስርአቱን በሐይል ለመፈታተን ከመከሩት የሁከት ሀይሎች ዋነኞቹ ነበሩ ማለት ይቻላል” ብሎአል።

ኢህአዴግ ከአክራሪዎች ጎን በመቆም አመጽ ለማነሳሳት ሞክረዋል ካላቸው ድርጅቶች መካከል ድምጻችን ይሰማ፣ ግንቦት 7 አሜሪካ ድምጽ ሬዲዮና ቢላል ሬዲዮ በዋናነት ተጠቅሰዋል።

በውስጡ ያሉ አንዳንድ የኢህአዴግ አመራሮችም እንዲሁ በሀማኖት ጉዳይ ጣልቃ እየገቡ ችግሩን እያባባሱ በመሆኑ፣ እነዚሁ ባለስልጣናት የመንግስትን ስልጣን አስረክበው ወደ ሰባኪነታቸው እንዲያመሩ እንመክራለን ብሎአል።

መጽሄቱ በኢትዮጵያ ውስጥ በክርስትና እና በእስልምና ሀይማኖቶች ውስጥ እየታየ ያለውን የአክራሪነት አዝማሚያና ይህን ተጠቅሞ የሚካሄደውን የፖለቲካ እንቅስቃሴ ለመግታት መንግስት በየትምህርት ተቋማት ትምህርቶችን መስጠት፣ ለወጣቶች ተገቢውን ስራ በመስጠትና አስፈላጊውን ህጋዊ እርምጃ መውሰድ እንደላበት ጠቁሟል።

ኢህአዴግ አሁን የሚታየው የሙስሊሙ እንቅስቃሴ እየተዳከመ ቢመጣም ተመልሶ ስርአቱን ሊገዳደር የሚችልበት ምልክት እየታየ መሆኑን ጠቁሟል።

በሌላ ዜና ደግሞ ኢህአዴግ የሚዲያ አደረጃጀቱን በአዲስ መልክ ማዋቀሩ ታውቋል። የፌደራል እና የክልል የመገናኛ ብዙሀንም ከእንግዲህ ወዲህ የኢህአዴግ ከፍተኛ አመራሮች በሚሰጡዋቸው አቅጣጫ ፕሮግራሞቻቸውን እንደሚያዘጋጁ ታውቋል። በደቡብ ክልል አቶ ሽፈራው ሽጉጤ፣ በአማራ ክልል አቶ አለምነው መኮንን፣ በኦሮምአ አቶ አለማየሁ አቶምሳ በየወሩ ከጋዜጠኞች እና ዋና አዘጋጆች ጋር በመተባበር የዜና ዘገባ አቅጣጫዎችን ይሰጣሉ።

ማንኛውም ጋዜጠኛ ስራውን የሚሰራው እነዚህ የኢህአዴግ አመራሮች በሚሰጡት የትኩረት አቅጣጫ መሰረት እንደሚሆን ከግንባሩ የቅርብ ሰዎች ያገኘነው መረጃ ያስረዳል።