ለኢራቅ ችግር የፖለቲካ መፍትሄ እንደሚያሻው የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ተናገሩ

ሰኔ ፲፯(አስራ ሰባት)ቀን ፳፻፮ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-ኢራቅን እየጎበኙ የሚገኙት ጆን ኬሪ ይህን የተናገሩት አይ ኤስ ኤስ እየተባለ የሚጠራው በአብዛኛው በሱኒዎች የተሞላው ተዋጊ ሃይል የሰሜን ኢራቅን አካባቢዎች እየተቆጣጠረ መምጣቱን ተከትሎ ነው። ድርጅቱ ከአልቃይዳ ጋር ግንኙነት አለው በሚል አሜሪካ እንደ አሸባሪ በመመልከቷ እውቅና አልሰጠችውም።

ጆን ኬሪ ኢራቃውያን የችግሩን አሳሳቢነት ተረድተው እየወሰዱት ያለው እርምጃ ሊደነቅ ይገባል አሉ ሲሆን፣ የኢራቅ ፖለቲከኞች በአስቸኳይ ፖለቲካዊ መፍትሄ እንዲፈልጉ ጠይቀዋል።

ዘገባዎች እንደሚያመለክቱት ጦርነቱ በሺአ እና በሱኒ የእስልምና ሃይማኖት ተከታዮች መካከል የሚደረግ ሲሆን፣ ሱኒዎች በሺአዎች በሚመራው የኑሪ አልማላቂ መንግስት በመገፋታቸው ጠመንጃ ለማንሳት ተገደዋል።

በብርሃን ፍጥነት ከተሞችን እየተቆጣጠሩ የመጡት ኤኢ ኤስ ኤስ ተዋጊዎች ወደ ባግዳድ እንደሚያቀኑም እየዛቱ ነው። ታጣቂዎቹ ባግዳድ አካባቢ ጦርነት የሚከፍቱ ከሆነ ከፍተኛ እልቂት ሊፈጠር እንደሚችል ታዛቢዎች ይናገራሉ።

ከዚሁ ጋር በተያያዘ ኩርዶች ከኢራቅ ተገንጥለው የራሳቸውን መንግስት የመመስረት ፍላጎታቸው ከፍ እያለ ነው።

የኢራቅ መንግስት ሳውድ አረቢያ አመጽያኑን ትረዳለች በማለት እየከሰሰ ሲሆን፣ ሱኒዎች ደግሞ የኢራንን ጣልቃ ገብነት አጥበቀው እየተቃወሙ ነው።  ኢራቅ እንደ ኢራን ሁሉ አብዛኛው ህዝብ የሺአ እምነት ተከታይ ነው።