የጸጥታ ሃይሎች የጸጥታ ስጋት እየሆኑ መምጣታቸው ተገለጸ

(ኢሳት ዲሲ–ጳጉሜ 5/2010)በየክልሉ ያሉ የጸጥታ ሃይሎች ከጸጥታ ማስከበር ይልቅ የጸጥታ ስጋት እየሆኑ መምጣታቸው ተገለጸ።

አንዳንድ ክልሎች በድንበር አካባቢ ታጣቂዎችን እያሰባሰቡ መሆናቸውንም የመከላከያ ሚኒስቴር ከፍተኛ ባለስልጣን ገልጸዋል።

በሃገር መከላከያ ሚኒስቴር የማዕከላዊ ዕዝ ዋና አዛዥ የሆኑት ሜጀር ጄኔራል ጌታቸው ጉዲና ይህንን የተናገሩት መቀሌ በተካሄደ የመከላከያ ሰራዊት ስብሰባ ላይ ነው።

የኢፌድሪ ፕሬዝዳንት ዶክተር ሙላቱ ተሾመና ጠቅላይ ኢታማዦር ሹሙ ጄኔራል ሰአረ መኮንን በተገኙበት ትላንት መቀሌ በተካሄደው ስብሰባ ላይ እንደተገለጸው ችግሩ በሰው ሕይወትና ንብረት ላይ ስጋትን ደቅኗል።

የማዕከላዊ ዕዝ ዋና አዛዥ ሜጄር ጄኔራል ጌታቸው ጉዲና እንደገለጹት የክልል የጸጥታ አካላት ለጋራ ሰላምና ደህንነት ከመትጋት ይልቅ ለሌላ ተግባር በመዘጋጀት ላይ ይገኛሉ።

እነዚህ ሃይሎች ውስጣዊ የጸጥታ ችግርን በመቆጣጠርም ረገድ ክፍተት የሚታይባቸው በመሆኑ የመከላከያ ሰራዊቱ ዋናው ተልዕኮው ላይ ብቻ እንዲያተኩር እንዳደረገው አመልክተዋል።

በአሁኑ ወቅት በአጎራባች ክልሎች ወሰን አካባቢ የታጠቀ ሃይል የማሰባሰብ ዝግጅት እየታየ ነው ብለዋል ጌታቸው ጉደታ።

ይህ ደግሞ ሕዝብ ላይ ስጋትን የደቀነ በመሆኑ የክልልም ሆነ የፌደራል መንግስቱ ትኩረት ሊሰጡት እንደሚገባ አሳስበዋል።

ይህ በድንበር አካባቢ የሚደረገው የክልል የጸጥታ አካላት መሰባሰብ በሰዎች ሕይወትና በንብረት ላይ ጉዳት ከማድረሱ በፊት አፋጣኝ የመከላከል ርምጃ እንዲወሰድም ጥሪ አቅርበዋል።