የኢትዮጵያ የመንገደኞች አውሮፕላን ከአየር ላይ ግጭት ተረፈ

የኢትዮጵያ የመንገደኞች አውሮፕላን ከአየር ላይ ግጭት ተረፈ
( ኢሳት ዜና መስከረም 01 ቀን 2011 ዓ/ም ) ዘ ኢስት አፍሪካን እንደዘገበው ባለፈው ረቡዕ የኢትዮጵያ አየር መንገድ ንብረት የሆነ ኢት 858፣ ቦይንግ 737-800 ከጣሊያኑ የሌዢር ኤርላይን ኒዮስ ቦይንግ 767-306 R የበረራ ቁጥር NOS 252 ጋር በኬንያ ሰማይ ላይ ለመጋጨት ሲቃረብ በአንድ ደቂቃ ልዩነት ተርፏል። አደጋ ተፈጥሮ ቢሆን ኖሮ በአለም አሰቃቂው የአውሮፕላን አደጋ ተብሎ ይመዘገብ እንደነበር ጋዜጣው ዘግቧል።
ከምሽቱ 3 ሰዓት ላይ የኢትዮጵያ አየር መንገድ ከደቡብ አፍሪካ ጆሃንስበርግ ከተማ ተነስቶ ወደ አዲስ አበባ በ37 ሺ ጫማ ከፍታ ላይ በመብረር ላይ የነበረ ሲሆን፣ በተመሳሳይ ቀን ምሽት 12 ሰዓት ላይ የጣሊያን አውሮፕላን ከቪሮና ተነስቶ ወደ ዛንዚባር በማምራት ላይ ነበር። እኩለ ሌሊት ላይ ሁለቱም አውሮፕላኖች ወደ ኬንያ አየር ክልል የገቡ ሲሆን፣ ሁለቱም ለግጭት በሚያደርሳቸው ሁኔታ ፊት ለፊት እየተጓዙ እንደነበር ጋዜጣው ዘግቧል።
የግጭት መቆጣጠሪያ መሳሪያው ለኢትዮጵያ አየር መንገድ የማስጠንቀቂያ መልዕክት እንዳስተላለፈ ፣ ፓይለቱ በአንድ ደቂቃ ውስጥ ወደ 38 ሺ ጫማ ከፍ በማድረግ እና ለ5 ደቂቃ በዚሁ ከፍታ ላይ በመቆየት አደጋ እንዳይፈጠር ለማድረግ ችሎአል።
የኬንያ አየር ተቆጣጣሪዎች የኢትዮጵያን የአየር ትራፊክ ተቆጣጣሪዎች ተጠያቂ አድርገዋል። የኢትዮጵያ የአየር ታረፊክ ተቆጣጣሪዎች እንደገለጹት የጣሊያን አየር መንገድ አስቀድሞ በምን ያክል ከፍታ እንደሚበር ሲገልጽ፣ የኢትዮጵያ አየር መንገድ ግን ይህን ባለማድረጉ አደጋው ሊደርስ እንደነበር ገልጸዋል።
የኢትዮጵያ የአየር ትራፊክ ተቆጣጣሪዎች አደጋው ከመድረሱ አራት ቀናት በፊት የስራ ማቆም አድማ አድርገው ነበር። ይህንን ተከትሎ የኬንያ አየር መንገድ ከ አዲስ አበባ የሚነሱና ወደ አዲስ አበባ የሚደረጉ በረራዎች ደህንነታቸው አስተማማኝ አለመሆኑን አስቀድሞ ማስጠንቀቂያ ልኮ እንደነበር ጋዜጣው አክሎ ዘግቧል።
የኢትዮጵያ ሲቪል አቬሽን ባለስልጣን በኬንያ በኩል የቀረበውን ክስ ውድቅ አድርጎታል። የኬንያ አየር ተቆጣጣሪ ያወጣው መግለጫ ሃሰትና መሰረተ ቢስ ነው ያለው የሲቪል አቬሽን ባለስልጣን፣ እንዲህ አይነት አደጋ ይከሰታል የሚል መረጃ ለኢትዮጵያአየር ተቆጣጣሪዎች አለመነገሩን ገልጿል።
የአየር ትራፊክ ተቆጣጣሪዎችን ለአድማ አነሳስተዋል የተባሉ 9 አመራሮችና ሰራተኞች መታሰራቸው ይታወቃል።