የትግራይ ተወላጆች ወደ አድዋና አካባቢው እየተመለሱ ነው ተባለ

(ኢሳት ዲሲ–መጋቢት 11/2010) ከአማራ ክልል ባህርዳር የትግራይ ተወላጆች ንብረታቸውን ሸጠው ወደ አድዋና አካባቢው እየተመለሱ መሆናቸውን የኢሳት ምንጮች ገለጹ።

በባህርዳር ኢትዮ ስታር ተብሎ በትግራይ ተወላጅ ንብረትነት  የሚታወቀውን ሆቴል የጎጃም አዴት ተወላጅ የሆኑትና  የሙሉጌታ ሪል ስቴት ባለቤት እንድገዙት  ታውቋል።

አባ አድጎይ ተብለው የሚታወቁትን ኤርትራዊ ቤተሰቦች በማፈናቀል ቦታውን በተጭበረበረ መንገድ በሊዝ የወሰደው የትግራይ ተወላጅም ይዞታውን ሸጦ መቀሌ ገብቷል።

ኢትዮ ስታር ሆቴል ከጣና ሃይቅ ትይዩ በሆነ ስፍራ ከአማራ ልማት ማህበር ጽሕፈት ቤት ፊት ለፊት የሚገኝ 6 ደረጃ ያለው የፎቅ ሕንጻ ነው።

የትግራይ ተወላጆች ንብረት የነበረውን ይህ ሆቴል ደንበኞች እየራቁት በመሄዱ ገቢው አሽቆልቁሎ እስከ መዘጋትም ደርሶ ነበር።

ከሕዝባዊ እምቢተኝነቱ ጋር ተያይዞ ሆቴሉ ከተዘጋ በኋላ የማሰቃያ ስፍራ ተደርጎም ወጣቶች ታፍነው ይታሰሩበት ነበርም ተብሏል።

ወ/ሮ መብራት ሃይሉ  በተባሉ የአድዋ ተወላጅ የተገነባውና ከእህቷ ወይዘሮ አወጣሽ ሃይሉ ጋር ሲያስተዳድሩት የነበረው ሆቴል በመጨረሻም ሙሉጌታ ሪል ስቴት በተባለ ኩባንያ መገዛቱ ተነግሯል።

ኢትዮ ስታር ሆቴል ከ60 ሚሊየን ብር በላይ ከተሸጠ በኋላ በባለቤትነት የሚያስተዳድሩት ወ/ሮ አወጣሽና ቤተሰቦቻቸው  ወደ ትግራይ አድዋ ሄደዋል።

ይህ በእንዲህ እንዳለም አባ አድጎይ ዳቦ ቤት የተባለውን  የኤርትራ ተወላጆች ንብረት በዝቅተኛ ሊዝ ዋጋ የገዛውና ይዞታውን እንዲፈርስ ያደረገው አቶ ዳንኤል የተባሉ  የትግራይ ተወላጅም በተመሳሳይ  ይዞታቸውን ሸጠው   ወደ መቀሌ መሄዳቸውም ነው የተነገረው።

የአባ አድጎይ ዳቦ ቤትን በመቶ ሺዎች በሚቆጠር ገንዘብ በሊዝ የወሰደት አቶ ዳንኤል ይዞታውን በ11 ሚሊየን ብር መሸጣቸውን  የአካባቢው ምንጮች ለኢሳት ገልጸዋል።

በባህርዳርና አካባቢው ሕዝባዊ እምቢተኝነት ከተጀመረ ወዲህ በከተማዋ አቡነ አረጋዊ በተሰኘ የጽዋ ማህበር ስም የተደራጁ አንዳንድ የትግራይ ተወላጆች ለሕወሃት ይሰልሉ እንደነበር መዘገቡ አይዘነጋም።

በዚሁም ምክንያት ከስርዓቱ  ቅርበት  አላቸው በሚባሉ የትግራይ ተወላጆች ጥቃት እንዳይደርስባቸው ጥበቃ ሲደረግላቸው ቆይቷል።

አንዳንድ በትግራይ ተወላጆች ይተዳደሩ የነበሩ የንግድ መደብሮችም የባለቤቶቹ ማንነት እንዳይታወቅ ስም እስከመቀየርም ደርሰው እንደነበር የኢሳት ምንጮች ገልጸዋል።