የመንጋ ፍትህና ስርአት አልበኝነት እየተስፋፋ ነው

(ኢሳት ዲሲ–መስከረም 9/2011) የመንጋ ፍትህና ስርአት አልበኝነት እየተስፋፋ ነው ሲል የሰብአዊ መብቶች ጉባኤ አሳሰበ።

የሰብአዊ መብቶች ጉባኤ  በቡራዪ በሰላማዊ ሰዎች ላይ የተፈጸመውን ግድያ ጨምሮ በሃገሪቱ የተለያዩ አካባቢዎች የሚታዩ ርምጃዎች አሳሳቢ መሆናቸውንም አመልክቷል።

ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አሕመድ ወደ ስልጣን መምጣታቸው ሐገሪቱ ተጋርጦባት የነበረውን አደጋ ያስታገሰና የዲሞክራሲ ጭላንጭል የፈነጠቀ ነው ሲልም ሰመጉ አስታውቋል።

ነሐሴ 9/2010 በደቡብ ክልል ሰካ ዞን ብሔርን መሰረት ባደረገ ግጭት ሶስት ሰዎች መገደላቸውንና ንብረት መውደሙን ገልጿል።

በመንግስት ሃይሎች ጣልቃ ገብነት ግጭቱ የበረደ ቢሆንም እንደገና አገርሽቶ ተጨማሪ ሁለት ሰዎች መገደላቸውን አሰብአዊ መብቶች ጉባኤ ባወጣው መግለጫ አመልክቷል።

በኦሮሚያ ክልላዊ መንግስት ባሌ ዞን ጎባ ከተማ የተደራጁ ወጣቶች ከነሐሴ 13 እስከ 16/2010 በፈጸሙት ጥቃት 10 ሰላማዊ ሰዎች መገደላቸውም ተመልክቷል።

በደቡብ ክልል በየም ልዩ ወረዳ ሐምሌ 15/2010 ሰልፍ የወጡ ነዋሪዎች መካከል በተከሰተ ግጭት 6 ሰዎች ሲገደሉ በርካታ ንብረት መውደሙን፣በዳውሮ ዞን ተርጫ ከተማ ነሐሴ 5 እና 6 በተካሄደ ሰልፍ ላይ በተነሳ ግጭት 5 ሰዎች መገደላቸውንና ንብረት መውደሙን ኢሰመጉ ገልጿል።

ነሐሴ 6/2010 የኦሮሞ ሚዲያ ኔትወርክ ሃላፊዎችን ለመቀበል ከፍተኛ ሕዝብ በተገኘበት ትዕይንት “ፈንጂ የጫነ ተሽከርካሪ መጣ” በሚል በተፈጠረ ግርግር ሶስት ሰዎች ተረጋግጠው ሲሞቱ አንድ ሰው ደግሞ ቦምብ ይዞ ተገኝቷል በሚል ተቀጥቅጦ መገደሉንና ተዘቅዝቆ መሰቀሉን ሰመጉ ገልጿል።

ከሐምሌ 28 እስከ 29/2010 በሶማሌ ክልል በተለያዩ ከተሞች በተለይም በጅጅጋ፣ዋርዴር፣ጎዴ፣ደጋሃቡር፣ፊቅ፣ቀላፎ በሔርን መሰረት ባደረገ በተመሳሳይ ቀንና ሰአት በተፈጸመ የተደራጀ ጥቃት ከ100 በላይ ሰዎች ሲገደሉ በርካቶች የአካል ጉዳት ደርሶባቸዋል።

6 አብያተ ክርስቲያናት ተቃጥለዋል፣በበርካታ የንግድ ቤቶችና በመኖሪያ ቤቶች ዝርፊያና ቃጠሎ ተፈጽሟል።

በድሬደዋ ከተማም በተመሳሳይ ግዜ ውስጥ 14 ሰዎች መገደላቸውንም ሰመጉ አስታውቋል።

በኦሮሚያ ክልል ምስራቅ ሃረርጌ ዞን በመዩ ሙለቱ ወረዳ ሮጊ ቀበሌ ማህበር ውስጥ የሶማሌ ክልል ልዩ ሃይል ነሃሴ 13/2010 በፈጸመው ጥቃት 31 ሰዎች በጥይት ተገድለዋል።

ነሐሴ 18/2010 በድሬደዋ ማረሚያ ቤት በተነሳ አመጽ 1 እስረኛ ሕይወቱ ሲያልፍ በ3 ፖሊሶችና በሶስት እስረኞች ላይ ከባድ ጉዳት መድረሱንም የሰመጉ ሪፖርት ይዘረዝራል።

የአማራ ማንነት ጥያቄ አንስታችኋል የተባሉ 85 ሰዎች ኮረም ላይ መታሰራቸውን የጠቀሰው የሰብአዊ መብቶች ጉባኤ ሐምሌ 11 እና 18/2010 ዋጃ ላይ ሶስት ሰዎች መገደላቸውን ነሐሴ 13/2010 ደግሞ ኮረም ላይ አንድ ሰው በገደሉን ዘርዝሯል።

ከዚሁ ጋር በተያያዘ በአላማጣ ወረዳ ከዋጃ፣ጥሙጋ፣ሰሌን ውሃ፣ቢትሙ፣ሃርሌ አየር ማረፊያና በአጎራባች ቀበሌዎች 285 ሰዎች በነሐሴ ወር ተፈናቅለው ራያና ቆቦ ውስጥ በአልማ ትምህርት ቤት መጠለላቸውን ገልጿል።

በደቡብ ክልል ጉራጌ ዞን በመስቃንና በማረቆ ማህበረሰብ መካከል ከቀበሌ ይገባኛል ጋር በተያያዘ መስከረም 3/2011 እንሶኔ ላይ 3 ሰዎች ሲገደሉ፣8 ሰዎች ደግሞ ቡታጅራ ላይ መገደላቸው ተመልክቷል።

በሳምንቱ መጨረሻ በቡራዩ፣በአሸዋ ሜዳና በከታ መንግስት ባረጋገጠው መሰረት ከ25 ሰዎች በላይ መገደላቸውን ሰመጉ አስታውሷል።

ሰኞ መስከረም 7/2010 አዲስ አበባ ላይ 5 ሰዎች በጸጥታ ሃይሎች መገደላቸውንም በመግለጫው አስፍሯል።

በተመሳሳይ ቀን በአርባምንጭ ከተማ 8 ሰዎችም በጥይት ሲመቱ፣የአንደኛው ሕይወት ማለፉንም አስታውሷል።

የቡራዩ የጥቃት ምስሎች የድርጊቱን አፈጻጸም ጭካኔ ብቻ ሳይሆን የተደራጁ ሃይሎች እየተጓዙበት ያለውን አደገኛ አቅጣጫ ያሳያል ብሏል።

“በከፍተኛ መስዋዕትነት የተገኘው የዲሞክራሲ ጭላንጭል ስር የሰደዱ ችግሮች እየተገዳደሩት ይገኛሉ” ያለው ሰመጉ፣መንግስት ሕገ ወጥነትንና ስርአተ አልበኝነትን በመቆጣጠር ረገድ ቸልተኝነት አሳይቷል ሲል ወቅሷል።

ይሕ ሕዝባዊ ቁጣ ፈጣን ምላሽ ካላገኘ ፍጹም ወደ ሆነ ስርአት አልበኝነት ላለምሽእገሩም ምንም አይነት ዋስትና የለም ኣኢልም አሳስቧል