በቤንሻንጉል ካማሽ ዞን ውጥረቱ ተባባሰ

(ኢሳት ዲሲ–መስከረም 18/2011) በቤንሻንጉል ጉምዝ ክልል ካማሽ ዞን ውጥረቱ መባባሱ ተገለጸ።

ከሶስት ቀናት በፊት የጀመረው ውጥረት አራት የካማሽ ዞን ባለስልጣናትና የጸጥታ አመራሮች መገደላቸውን ተከትሎ እየተባባሰ መምጣቱን የደረሰን መረጃ ያመለክታል።

አራቱ አመራሮች ባልታወቁ ታጣቂዎች በተወሰደ ርምጃ መገደላቸው የጉምዝ ብሔረሰብ ተወላጆችን ማስቆጣቱን የጠቀሱት የኢሳት ምንጮች በንጹሃን ነዋሪዎች ላይ የበቀል ርምጃ በመወሰድ ላይ መሆኑን ገልጸዋል።

በሺዎች የሚቆጠሩ የአማራና የኦሮሞ ተወላጅ የሆኑ የካማሽ ዞን ነዋሪዎች አካባቢውን ጥለው በመሰደድ ላይ መሆናቸውም ታውቋል።

ባለፈው ማክሰኞ የኦሮሚያና የቤንሻንጉል ጉምዝ ክልል አመራሮች ስብሰባ ተቀምጠው ነበር።

በሁለቱ ክልሎች መካከል የሰላምና የጸጥታ ጉዳዮች ላይ የተነጋገሩት አመራሮች ስብሰባውን አጠናቀው ሲመለሱ ካማሼ ዞን ውስጥ ኪንጊ በተባለ ስፍራ ጥቃት ተፈጸመ።

ባልታወቁ ሃይሎች በተፈጸመው በዚሁ ጥቃት ከካማሼ ዞን አራት አመራሮች ሲገደሉ ሁለት ይቆስላሉ።

የቤንሻንጉል ጉምዝ ክልል ፖሊስ  ጸረ ሰላም ሃይሎች ከማለት ውጭ ስለጥቃት አድራሾቹ ዝርዝር ማብራሪያ መስጠት አልቻለም።

የተገደሉት በሙሉ የካማሼ ዞን አመራሮች መሆናቸውን የጠቀሱት ምንጮች በህወሀት የተቀነባበረ ጥቃት ሊሆን እንደሚችል ገልጸዋል።

የመከላከያ ሰራዊት ወደ አከባቢው ያመራ ሲሆን ያልታወቁ የተባሉ ታጣቂዎችን ለመያዝ እያሰሰ መሆኑን የክልሉ ፖሊስ አስታውቋል።

አራቱ የካማሼ ዞን አመራሮች መገደላቸውን ተከትሎም አከባቢው ውጥረት ነግሶበት አራተኛ ቀኑን መያዙን የኢሳት ምንጮች ገለጸዋል።

በተፈጸመው ጥቃት የተቆጡ የጉምዝ ብሄር ተወላጆች የበቀል እርምጃ እንወስዳለን በማለታቸው በካማሼ ዞን በተለያዩ አከባቢዎች የሚኖሩ የአማራና የኦሮሞ ተወላጆች በስጋት እየተሰደዱ መሆኑን ነው ለማወቅ የተቻለው።

በካማሼ ዞን በሚገኙ አምስቱ ወረዳዎች የሚገኙ ነዋሪዎች ቤታቸውን ዘግተው ንብረታቸው ትተው ወደ አጎራባች አከባቢዎች በመሸሽ ላይ መሆናቸውን የደረሰን መረጃ ያመለክታል።

በካማሽ፣ ሎጅጋንፎይ፣ በያሶና በሌሎች ወረዳዎች ያለው የጸጥታ ሁኔታ ስጋት ላይ የሚጥል ነው ያሉት ነዋሪዎች መንግስት በቶሎ ካልደረሰ በህይወት ላይ ከፍተኛ ጉዳት ሊደርስ እንደሚችል አስጠንቅቀዋል።

ሁኔታውን ለሚመለከተው አካል ብናሳውቅም ወታደር እንካለን በሚል ተስፋ እንድንቆይ ይመክሩናል ያሉት ነዋሪዎች ከመንግስት የመሳሪያ ግምጃ ቤት መሳሪያ በመዝረፍ የታጠቀው የአከባቢው ሰው አደጋ ሊጥልብን ተዘጋጅቷል ሲሉ ስጋታቸውን ገልጸዋል።

በአንዳንድ አካባቢዎች ነዋሪው ከቤት ሳይወጣ ቀናት እንዳለፉትም እየተገለጸ ነው።

ዘግይተው የሚደርሱን መረጃዎች እንደሚያመለክቱትም በካማሼ ዞን ሁኔታው ተባብሶ ሰዎች እየተገደሉ ነው።

መንግስት በአስቸኳይ እንዲደርስላቸውም ነዋሪዎች ጥሪ አድርገዋል።