ለኢሬቻ በአል የሚመጡ ታዳሚዎች ከተለያዩ ነገሮች እንዲቆጠቡ ተጠየቀ

(ኢሳት ዲሲ–መስከረም 18/2011)ለኢሬቻ በአል የሚመጡ ታዳሚዎች ፖለቲካን የሚያንጸባርቅ ማንኛውንም አርማም ሆነ ሰንደቅ አላማ ከመያዝና ዘፈን ከመዝፈን እንዲቆጠብ የኦሮሚያ ክልላዊ ፕሬዝዳንት አሳሰቡ።

ፕሬዝዳንቱ አቶ ለማ መገርሳ የኢሬቻ በአልን አስመልክተው ባስተላለፉት የእንኳን አደረሳችሁ መልዕክት በአሉ በሰላም እንዲጠናቀቅ የክልሉ መንግስት አስፈላጊውን ዝግጅት አድርጓል ብለዋል።

የኢሬቻን በአል በዩኔስኮ ለማስመዝገብ እንቅስቃሴ መጀመሩንም አቶ ለማ መገርሳ ገልጸዋል።

በሌላ በኩል ላለፉት ስምንት አመታት በስልጣን ላይ የቆዩት አባ ገዳ በየነ ሰንበቶ የስልጣን ዘመናቸው በማብቃቱ ለአዲስ አባገዳ ቦታውን መልቀቃቸው ተገልጿል።

አዲሱ አባገዳ ጎበና ሆላ እሬሶ ስልጣናቸውን ነገ በይፋ እንደሚረከቡ የደረሰን መረጃ አመልክቷል።

አመታዊው የምስጋና ቀን ኢሬቻ የፊታችን እሁድ በቢሾፍቱ ሆራ አርሴዴ በድምቀት ይከበራል።

በአሉ በሰላም ተጀምሮ እንዲጠናቀቅ በኦሮሞ አባ ገዳዎችና በኦሮሚያ ክልል የጸጥታ ሃይሎች መካከል ንግግር መካሄዱም ተመልክቷል።

በኦሮሞ ባህል በየአመቱ በመስከረም ወር የሚከበረው የኢሬቻ በአል በዚህ በያዝነው 2011 አመተ ምህረት በከፍተኛ ድምቀት እንዲከበር ከፍተኛ ዝግጅት መደረጉን ለመገናኛ ብዙሃን የገለጹት የኦሮሞ ተሰናባቹ የአባገዳዎች ሊቀመንበር አባገዳ በየነ ሰንበቶ ናቸው።

የኦሮሚያ ክልላዊ መንግስት ፕሬዝዳንት አቶ ለማ መገርሳ በዓሉን አስመልከተው የእንኳን አደረሳችሁ መልዕክት አስተላልፈዋል።

ለክብረ በዓሉ የሚመጡ ሰዎች ፖለቲካን የሚያንፀባርቅ ማንኛው አርማ፡ሰንደቅ አላማ ከመያዝና ዘፈን ከመዝፈን መቆጠብ ይኖርበታል ሲሉም ርዕሰ መስተዳድር ለማ መገርሳ አሳስበዋል።

የእሬቻ በዓል በሰላም እንዲከናወን መንግስት ከአባገዳዎች ጋር በጥምረት እየሰራ መሆኑን የገለጹት አቶ ለማ መገርሳ መንግስት በዓሉ በሰላም እንዲጠናቀቅ አስፈላጊውን ዝግጅት ማድረጉን ጠቅሰዋል።

የኢሬቻን በዓል በአለም አቀፍ ትምህርት፡ ሳይንስ እና ባህል ተቋም ዩኒስኮ በቅርስነት ለማመዝገብ እየተሰራ መሆኑንም አቶ ለማ መገርሳ አስታውቀዋል።

የዛሬ ሁለት ዓመት በኢሬቻ በዓል ላይ በደረሰ አደጋ በርካታ ሰዎች መገደላቸው የሚታወስ ሲሆን በመላው ዓለም ኢትዮጵያውያን በተፈጸምው ግድያ ቁጣቸውን በመግለጽ በየዓመቱ ዕለቱን እያሰቡት ይገኛሉ።

በተያያዘ ዜና የፊታችን ዕሁድ የሚከበረውን የኢሬቻ በዓል በማስመልከት የአዲስ አበባ ወጣቶች በዓሉ የሚከበርበትን ቦታ ማጽዳታቸውን የኦሮሚያ ብሮድካስቲንግ ኔትወርክ ዘግቧል።

ከአዲስ አበባ በበጎ ፈቃደኛነት የሄዱት ወጣቶች ከቢሾፍቱ ከተማ ወጣቶች ጋር በመሆኑን የበዓሉን ስፍራ ማጽዳታቸውን ነው ዘገባው የሚያመለክተው።

ይህ በእንዲህ እንዳለም ላለፉት ስምንት ዓመታት የአባ ገዳዎች ሊቀመንበር በመሆን ያገለገሉት አባገዳ በየነ ሰንበቶ የስልጣን ዘመናቸው በማብቃቱ ለተተኪው አባገዳ እንደሚያስረክቡ ተገለጸ።

በነገው ዕለት የአባ ገዳ ሊቀመንበር በመሆን የሚያገለግሉት አባገዳ ጎበና ሆላ ለሚቀጥሉት ስምንት አመታት ስልጣኑን ለመያዝ ከተሰናባቹ አባ ገዳ ርክክብ እንደሚፈጽሙ የደረሰን መረጃ ያመልክታል።

በሌላ በኩል የመጀመሪያ የኢሬቻ የሰላም ሽልማት ተሰጠ።  በዛሬው ዕለት በተከናወነው  የሽልማት ስነ ስርዓት ሀገሪቱ ሰላም እንድትሆን ለተጉ ኢትዮጵያውያን ባለውለታዎች የሰላም ሸልማት ተበርክቶላቸዋል።

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ፓትሪያሪኮች ብጹዕ አቡነ ማቲያስ እና ብጹዕ አቡነ መርቆሪዮስ፣ አባ ገዳ በየነ ሰንበቶ፣ የኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት ሐጂ ኡመር እድሪስ፣ የጋሞ የሀገር ሽማግሌዎች የመጀመሪያው የኢሬቻ የሰላም ሽልማት ተሸላሚ መሆናቸው ታውቋል።

በኪነ ጥበብ ዘርፍ ጽምጻዊ አሊ ቢራ ድምጻዊ መሃሙድ አህመድ እና አርቲስት ለማ ጉያ የኢሬቻ የሰላም ሽልማት መቀበላቸውን የኦሮሚያ ብሮድካስቲንግ ኔትወርክ ዘግቧል።