የብሪታኒያ ፓርላማ አባላት በአንዳርጋቸው ጽጌ ጉዳይ ላይ ስለሚወሰደው ዕርምጃ ክርክር ሊያካሄዱ ነው

ኢሳት (ታህሳስ 6 ፥ 2009)

የብሪታኒያ መንግስት በአቶ አንዳርጋቸው ፅጌ ጉዳይ ዙሪያ መውሰድ በሚገባው ዕርምጃ ላይ ለመምከር የሃገሪቱ የፓርላማ አባላት በቀጣዩ ሳምንት የክርክር መድረክ ሊያካሄዱ መሆኑ ተገለጸ።

ካለፉት ጥቂት ወራት ጀምሮ አቶ አንዳርጋቸው በብሪታኒያ መንግስት ተወካዮች ዘንድ እንዲጎበኝ መደረጉ በፓርላማ አባላትና በሰብዓዊ መብት ተሟጋቾች ዘንድ ስጋትን ማሳደሩን የተለያዩ አካላት በመግለጽ ላይ ናቸው።

የጉዳዩ አሳሳቢነትን ተከትሎ የብሪታኒያ የፓርላማ አባላት የሃገሪቱ መንግስት መውሰድ በሚገባቸው እርምጃዎችና የዲፕሎማሲያዊ ጥረቶች ዙሪያ ለመምከር የፊታችን ማክሰኞ ልዩ የክርክር መድረግ ማዘጋጀቱን ሪፖሪቭ የተሰኘ የብሪታኒያ የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ተቋም ሃሙስ አስታውቋል። andargachew-tisge

የአቶ አንዳርጋቸው ፅጌ ጉዳዩን በመከታተል ላይ የሚገኘው ይኸው ድርጅት የአቶ አንዳርጋቸው ወቅታዊ ሁኔታ እጅጉን አሳሳቢ እየሆነ መምጣቱን ገልጿል።

ከወራት በፊት አቶ አንዳርጋቸውን የጎበኙ የብሪታኒያ መንግስት ተወካዮች አቶ አንዳርጋቸው ፅጌ ለደህንነቴ ስጋት አድሮብኛል ሲሉ ያሉበትን አሳሳቢ ሁኔታ እንዲጋሯቸው ይፋ ማድረጋቸው ይታወሳል።

ይሁንና የሃገሪቱ ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ለኢትዮጵያ ባለስልጣናት ጉዳዩን አስመልክቶ ማብራሪያን ቢጠይቅም ለወራት ያህል ምላሽ ሳያገኝ መቅረቱን ለመረዳት ተችሏል። ይህንንም ተከትሎ የብሪታኒያ የፓርላማ አባላት በቀጣይ መውሰድ በሚገባቸው ዕርምጃዎች ዙሪያ በተያዘው የክርክር መድረክ ቀን ሰፊ ውይይትን ያካሄዳሉ ተብሎ ይጠበቃል።

በብሪታኒያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የፓርላማ ተወካይ የሆኑት ቶቢያስ ኤልሙድ አቶ አንዳርጋቸው ፅጌ ከቤተሰቦቻቸው ጋር የስልክ ግንኙነት እንዲያደርጉ በሃገራቸው መንግስት በኩል ጥያቄ መቅረቡን አስታውቀዋል።

እንደ ፈረንጆቹ አቆጣጠር በታህሳስ ወር 2014 አም አቶ አንዳርጋቸው ለተወሰነ ደቂቃ ቤተሰቦቻቸውን አግኝተው እንደነበር የሚታወስ ሲሆን፣ የብሪታኒያ ባለስልጣናት በዚሁ ጉዳይ ዙሪያ በመምከር ላይ መሆናቸውም ተገልጿል።

የብሪታኒያ ባለስልጣናት በአቶ አንዳርጋቸው ጽጌ የደህንነት ጉዳይ ስጋታቸውን በመግለጽ ላይ ቢሆኑም የኢትዮጵያ ባለስልጣናት እስካሁን ድረስ ምላሽን ከመስጠት ተቆጥበዋል።

ሪፕሪቭ የተሰኘው የሃገሪቱ የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ድርጅት በኢትዮጵያ ተግባራዊ ተደርጎ የሚገኘው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ለአቶ አንዳርጋቸው ስጋትን አሳድሮ እንደሚገኝ በተደጋጋሚ ሲገልጽ ቆይቷል።