ዜጎች ሀሳባቸውን በመግለጣቸው አሸባሪ እየተባሉ በመታሰር ላይ ናቸው ሲሉ ብቸኛ የተቃዋሚ ፓርቲ ተወካይ ተናገሩ

ጥር 30 ቀን 2004 ዓ/ም
ኢሳት ዜና:-99 በመቶ የአንድ ፓርቲ ሰዎች በታጨቁበት ፓርላማ ብቸኛ የተቃዋሚ ፓርቲ ተወካይ የሆኑት አቶ ግርማ ሰይፉ ዛሬ የአቶ መለስ ዜናዊን የስድስት ወራት ሪፖርት ካደመጡ በሁዋላ በርካታ ጥያቄዎችንና አስተያየቶችን ማቅረባቸውን ዘጋቢያችን ገልጧል።
ዜጎች ሀሳባቸውን በገለጡ አሸባሪ ይባላሉ በዚህም የተነሳ የፖለቲካ መህዳሩ እየጠበበ መምጣቱን አቶ ግርማ ተናግረዋል።
አቶ መለስ ዜናዊ የኢትዮጵያ የሽብርተኝነት ህግ በዓለም ላይ ምርጥ ከተባሉት ህጎች የተቀዳ መሆኑን፣ ሰዎች በህጋዊ ፓርቲ ሽፋን የሽብር ተግባር ለመፈጸም ሲንቀሳቀሱ መያዛቸውን ተናግረዋል።
የአሜሪካ ዲፕሎማቶችና የተባባሩት መንግስታት ድርጅት የሰብአዊ መብት ኮሚሽን የኢትዮጵያ የጸረ ሽብርተኝነት ህጉ እንዲሻሻል በቅርቡ መጠየቃቸውን መዘገባችን ይታወሳል።
በሌላ ደግሞ እየተወሰደ ያለው ተደራራቢ እርምጃ ህዝቡን እያስመረረ ነው፣ ይህ ለምን ይሆናል የሚል ጥያቄ ለአቶ መለስ ቀርቦ ነበር።
አቶ መለስ መንግስት የሚወስደው እርምጃ ድሀውን ለመጥቀም ብሎ መሆኑን ተናግረዋል።