አቶ አየለ ጫሚሶ በሕገወጥ ዶላር ምንዛሪ ለመጠቀም ሞክረው ባለመሳካቱ ግብረአበሮቻቸውን በወንጀል ከሰሱ

ጥቅምት ፩ (አንድ) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም

ኢሳት ዜና:-የቀድሞ ቅንጅት ለአንድነትና ለዴሞክራሲ ፓርቲ ሕጋዊ ወራሸ እኔ ነኝ የሚሉት አቶ አየለ ጫሚሶ ፎርጅድ ገንዘብ
በማዘዋወር ወንጀል ውስጥ ተሳትፈው በተፈጠረ አለመግባባት ጉዳዩን ወደፖሊስ ወስደው ራሳቸው ነጻ የሆኑበት
የሕገወጥ ገንዘብ ዝውውር የወንጀል ድርጊትን አንዳንድ የፖሊስ አባላት ተቃወሙት ፡፡

አቶ አየለ ጫሚሶ ኦልበሞ መስከረም 12 ቀን 2005 ዓ.ም በአዲስ አበባ  ቦሌ ክ/ከተማ ፖሊስ መምሪያ
ቀርበው በሁለት ተከሳሾች ማለትም በአቶ ተመስገን ወልዴ እና በታንዛኒያዊው ሚስተር ዊሊያም ከሌሽ  ተጭበርብሬአለሁ በሚል ክስ አቅርበዋል፡፡

የክሱ መዝገብ እንዲህ ይላል ”  ማክሰኞ መስከረም 8 ቀን 2005 ዓ.ም ከጠዋቱ 2፡30 ሰዓት አካባቢ 1ኛ ተከሳሽ አቶ ተመስገን ወልዴ በቀድሞ ወረዳ 2 ቀበሌ 09 የቤት ቁጥር 160 በሆነው የቅንጅት ፓርቲ ጽ/ቤት የነጣ እና ጥቁር ቀለም ያለው በወረቀት ላይ የታተመ የአሜሪካን ዶላር ይዞ መጥቶ ፤ “ሚስቴ ሁለት ሻንጣ ጥቁር ዶላር ከጅቡቲ ልካልኛለች፡፡ሁለት ጠርሙስ የዶላር ማጠቢያ ኬሚካልም መጥቷል ፤ይህንንም ዶላር በኬሚካል የሚያጥበው ታንዛኒያዊ ዜግነት ያለው ግለሰብ መሆኑን ነግሮኝ ግለሰቡን
በስልክ እንዳነጋግረው ገለጸልኝ፡፡ ይህንኑ ገንዘብ በአንድ ቀን 100 ዶላር፣በሌላ ቀን 200 ዶላር ባንክ ቤት መንዝረው አንድ ሺ ብር ለነዳጅ ይሁንህ ብለው ሰጥተውኛል ሲሉ በክሳቸው ላይ ጠቅሰዋል፡፡

ከዚህ በኃላም ግለሰቡ ዶላሩን ለማባዛት ቤት መከራየት ስላለብን ለኪራይ የሚሆን ገንዘብ በብድር እንድሰጣቸውና
ገንዘቡን ከ30 በመቶ ወለድ ጋር ዶላሩን አትመን ስንጨርስ እንመልሳለን ብለው 44 ሺ ብር ለሚስተር ዊሊያም
ሰጥቼው ገንዘቡን ቆጥሮ ለአቶ ተመስገን ሰጥቶታል፡፡ በተመሳሳይ ሁኔታ ተጨማሪ 900 ሺ ብር ጠይቀውኝ
ሰጥቻለሁ፡፡ለሶስተኛ ጊዜ መስከረም 10 ቀን ገንዘብ እንድሰጣቸው ሲጠይቁኝ ነገሩን መጠራጠር ጀመርኩኝ
ብለዋል፤በማመልከቻቸው፡፡

ለወሰዳችሁት ገንዘብ ፈርሙልኝ ብያቸው 1ኛ ተከሳሸ ሲፈርም 2ኛ ተከሳሸ አልፈርምም ብሎኛል ያሉት አቶ አየለ ጫሚሶ በደረሰባቸው መጭበርበር ተከሳሾቹ ከአገር ሳይወጡ ለህግ እንዲቀርቡላቸው ጠይቀዋል፡፡

የአቶ አየለን ክስ የተቀበለው የቦሌ ክ/ከተማ ፖሊስ ሁለቱን ግለሰቦች ተከታትሎ በቁጥጥር ሥር ሲያደርግ ለሕገወጥ ሥራው ተባባሪ የሆኑትን አቶ አየለ ጫሚሶን ነጻ ማድረጉ አግባብ እንዳልሆነ የፖሊስ ምንጮች ጠቅሰዋል፡፡ምንጮቹ እንዲህ ዓይነት በአገር ኢኮኖሚ ላይ ግልጽ ደባ ሲፈጸም ነገሩን ለፖለቲካ ጥቅም በማዋል አቶ አየለን ነጻ ማድረግ አሳፋሪ ተግባር ነው በማለት የፖሊስን ድርጊት አውግዘዋል፡፡

አቶ አየለ ከዚህ ቀደም የኢትዮጽያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ የቀድሞ ዋና ጸሐፊ የአቶ ተስፋዩ መንገሻ ፊርማ በማስመሰል
ኢህአዴግ በቦርዱ በኩል ለሚፈልጋቸው ፓርቲዎች እንዲከፋፈል የሰጠውን ገንዘብ ለግል ጥቅማቸው ለማዋል በማሰሰብ
መጠኑ አነስተኛ ገንዘብ ቦርዱ እንደለቀቀላቸው በማስመሰል ሕገወጥ ደብዳቤ አዘጋጅተው እጅ ከፍንጅ ቢያዙም
ከተግሳጽ ባለፈ ሕጋዊ እርምጃ ሳይወሰድባቸው ቀርቶአል፡፡

አቶ አየለ በምርጫ 97 ወቅት የገዢው ፓርቲ ደጋፊ በመሆን ቅንጅትን በማፍረስ እንደሚተቹ ይታወቃል።