አቶ አባዱላ ገመዳ መኖሪያቸውን እንዲለቁ መገደዳቸው ተሰማ

(ኢሳት ዜና–መስከረም 29/2010) የአፈጉባኤነት ስልጣናቸውን በፈቃዳቸው ለመተው መልቀቂያ ያቀረቡት አቶ አባዱላ ገመዳ መኖሪያቸውን እንዲለቁ መገደዳቸውን ምንጮች ገለጹ።

ዛሬ በፓርላማ በመደበኛ ስራቸው ላይ የታዩት አቶ አባዱላ ገመዳ ሃላፊነታቸውን ለመልቀቅ መወሰናቸውንም ትላንት አረጋግጠዋል።

ላለፉት አስር አመታት በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አፈጉባኤነት የቆዩት አቶ አባዱላ ገመዳ ከኦሮሚያና ከሶማሌው አዋሳኝ ድንበር ግጭት ጋር በተያያዘ የጸጥታ ሃይሉ ሚና እንዳላስደሰታቸውና ስልጣን ለመልቀቅም ምክንያት እንደሆናቸው አዲስ ስታንዳርድ ቢገልጽም እርሳቸው ግን ለዚህ ጉዳይ ማረጋገጫም ሆነ ማስተባበያ ከመስጠት ተቆጥበዋል።

አባዱላ ገመዳ ስልጣናቸውን ለመልቀቅ የፈለጉበትን ምክንያት ግን ወደፊት ጥያቄያቸው ተቀባይነት ሲያገኝ እንደሚገልጹ ተናግረዋል።

መልቀቂያ ማቅረባቸውን ተከትሎ የመንግስት ቤቶች ኤጀንሲ የያዙትን ቤት እንዲለቁ በማስገደዱ ማክሰኞ ቤቱን ያስረከቡ ቢሆንም ቤት ባለማግኘታቸው ጓደኞቻቸው ጋር ለመጠጋት መገደዳቸውን አዲስ ፎርቹን ከአዲስ አበባ ዘግቧል።

ቅዳሜ እለትም ቦሌ መንገድ አካባቢ ቤት ተከራይተው ወደዚያ መዛወራቸውም ታውቋል።

ስልጣን ላይ ያለው ቡድን የስልጣን መልቀቂያቸውን ጥያቄ ሳይቀበልና ስልጣናቸውን ሳይለቁ ቤታቸውን እንዲለቁ ያደረገበት ምክንያት ግልጽ አልሆነም።