አርበኞች ግንቦት7 በተለያዩ ከተሞች የተሳካ ስብሰባ ማድረጉን አስታወቀ

የካቲት ፮ ( ስድስት )ቀን ፳፻፱ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-የህወሃት/ኢህአዴግን አገዛዝ በሁለገብ ትግል ለማስወገድ እየታገለ ያለው አርበኞች ግንቦት7 ባለፈው ቅዳሜና እሁድ 46 ከተሞችን ያሳተፈ ስብሰባና የድጋፍ ማሰባሰብ ስራ መስራቱን ታውቋል።
የአርበኞች ግንቦት7 ሊ/መንበር ፕ/ር ብርሃኑ ነጋ በምስል ስልክ በተለያዩ አህጉራት ለሚገኙ ኢትዮጵያውያን በቀጥታ ንግግር ያደረጉ ሲሆን፣ ከሁሉም አካባቢዎች ለተነሱላቸው ጥያቄዎችም መልስ ሰጥተዋል። ፕ/ር ብርሃኑ ድርጅታቸው ስላለበት ወቅታዊ ሁኔታ፣ ከተለያዩ ድርጅቶች ጋር ስለሚያደርገው ትብብር እንዲሁም ስለኢትዮጵያ ወቅታዊ ሁኔታ ረጅም ሰአታት የፈጀ ገለጻ አድርገዋል።
የንቅናቄው ታጋዮችም በቪዲዮ የተቀረጹ መልዕክቶችን ለተሰብሳቢዎች አስተላልፈዋል። በሁሉም ስብሰባዎች ላይ የነበረው የህዝቡ ስሜት ከፍተኛ እንደነበር ውይይቶችን የተከታተሉት ዘጋቢዎቻችን ገልጸዋል።
በርካታ ከተሞችን በአንድ ጊዜ በማሳተፍ በአይነቱ የመጀመሪያ በሆነው በዚህ ዝግጅት ንቅናቄው የተሳካ የገቢ ማሰባሰብ ስራ መስራቱን ለኢሳት ገልጿል።