አርበኞች ግንቦት 7ትን ሊቀላቀሉ ሲሉ መያዛቸው የተገለጸው ተከሳሾች የመከላከያ ምስክሮቻቸውን ሳያቀርቡ ቀሩ

ሚያዚያ ፳፮(ሃያ ስድስት) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- በብርሃኑ ተክለያሬድ መዝገብ ስር የሚገኙት ብርሃኑ ተክለያሬድ፣ ፍቅረ ማርያም አስማማውና እየሩሳሌም ተስፋው ፣ ሚያዚያ 26፣ 2008 ዓም ከፍተኛው ፍርድ ቤት የቀረቡ ቢሆንም፣ ምስክሮቻቸውን አቅርበው ማሰማት ሳይችሉ ቀርተዋል። በበቂ ሁኔታ ሊከላከሉልን ይችላሉ ያሉዋቸው ምስክሮች ቃሊቲ እስር ቤት ሊያስወጣቸው ፈቃደኛ ባለመሆኑ መሆኑን እስረኞቹ ገልጸዋል።
አቶ ብርሃኑ ፤ እራሳቸውን ችለው እየተከራከሩ መሆናቸውን ገልጸው፣ እንዲቀርቡላቸው የሚፈልጉዋቸውን ምስክሮች የቃሊቲ ማረሚያ ቤት ሊያቀርብ አለመቻሉን አክለዋል።
እነ አቶ ብርሃኑ በመከላከያ ምስክርነት ከጠሩዋቸው ሰዎች መካከል በእስር ላይ የሚገኙት አቶ አንዳርጋቸው ጽጌ ፣ ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ ፣ ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ ፣ እንደሁም ጠበቃ ተማም አባቡልጉ፣ ኢንጂነር ይልቃል ጌትነት ፣ ፕሮፌሰር መስፍን ወልደማርያምና ዶ/ር መረራ ጉዲና የሚገኙበት ሲሆን፣ ከኢህአዴግ ከፍተኛ ባለስልጣናት መካከል ደግሞ አቶ በረከት ስምኦን፣ ዓባይ ፀሐዬ፣ ስብሀት ነጋ ፣ አዲሱ ለገሰ፣ ተፈራ ዋልዋ፣ ጄነራል ሳሞራ የኑስን ፣ ዶ/ር ደብረ ጺዮን ይገኙበታል።
የቃሊቲ እስር ቤት የመከላከያ ምስክሮቹን ማቅረብ ያልቻለው በአጃቢ እጥረት ነው የሚል መልስ ሲሰጥ፣ በሚቀጥለው ቀጠሮ ይዞ እንደሚቀርብ አስታውቋል። ፍርድ ቤቱ ለመንግስት ከፍተኛ ሀላፊዎች መጥሪያ በፖስታ ቤት እንዲላክላቸው እና ከግንቦት 30 እስከ ሰኔ.8/2008 ዓ.ም ምስክሮችን የማስማት ሂደት እንዲከናወን ውሳኔ አስተላልፏል።
በአቶ ዘላለም ወርቃገኘሁ መዝገብ የተከሰሱት የህሊና እስረኞች ቀደም ብለው አቶ አንዳርጋቸው ጽጌን በመከላከያ ምስክርነት እንዲቀርቡላቸው ጠይቀው የነበረ ቢሆንም፣ እስር ቤቱ ሊያቀርባቸው ፈቃደኛ ሳይሆን በመቅረቱ ሳይቀርቡ የፍርድ ቤቱም ትእዛዝ በአየር ላይ ቀርቷል። የቀድሞው የህወሃት ታጋይና የአረና ትግራይ አባሉ አቶ አስገደ ገብረስላሴም እንዲሁ የመንግስት ከፍተኛ ባለስልጣኖችን በመከላከያ ምስክርነት ጠርተዋቸው የነበረ ቢሆንም፣ በሰበብ አስባብ ሳይቀርቡላቸው ቀርቷል።
እነ አቶ ብርሃኑ የጠሩዋቸው ከፍተኛ የመንግስት ሹሞች ይገኛሉ ተብሎ አይጠበቅም። በተለይም ደብዳቤው በፖስታ እንዲደርሳቸው መባሉ ተጠያቂነት እንዳይኖር የሚያደርግ በመሆኑ፣ ባለስልጣኖቹ አልደረሰንም ለማለትና እስር ቤቱም ሲጠየቅ ሃላፊነቴን ተወጥቻለሁ በማለት ድራማውን ለማሳመር ይጠቅማል ሲሉ አስተያየት ሰጪዎች ይናገራሉ።
በተመሳሳይ የእስር ዜና በቂሊንጦ በእስር ላይ የሚገኙት ወርቁ ተረፈ ፣ ሰጠኝ ቢልልኝና አብርሃም ሞገሰ ፍርድ ቤት ቀርበው የነበረ ሲሆን፣ አቶ ወርቁ “ አማራ በመሆናችን ብቻ ሽብረተኞች እንባላለን፣ በድብደባ፣ ህክምና በመከልከልና በተለያዩ የማሰቃያ ዘዴዎች እየተቸገርን ነው። ችግራችን የሚሰማልን አጥተናል፣ ለማን አቤት እንበል” ሲሉ ፍርድ ቤት አቤቱታቸውን በማቋረጥ ለግንቦት14 ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል።