በጎንደር አንድ የገዢው ፓርቲ ንብረት የሆነ ተሳቢ የጭነት መኪና በቦንብ ተመታ

ጥር ፲፯ ( አሥራ ሰባት )ቀን ፳፻፱ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- ዛሬ ረቡዕ ከንጋቱ 11 ሰዓት ላይ ከጎንደር ወደ መቀሌ እቃ ጭኖ ሲጓዝ የነበረ አንድ የጭነት ተሽከርካሪ ከከተማው በ10 ኪ/ሜ ርቀት ላይ በምትገኘዋ ወለቃ በምትባለዋ መለስተኛ መንደር ላይ ሲደርስ በቦንብ በመመታቱ መኪናው እስከነጭነቱ ሙሉ በሙሉ በእሳት ተያይዞ ወድሟል።
ምንጮች እንደገለጹት ተሽከርካሪው ሌሊት ጎንደር ላይ እቃዎችን በመጫን ወደ መቀሌ ጉዞ በማድረግ ላይ ነበር። አስቀድሞ መረጃ የደረሳቸው ማንነታቸው ያልታወቁ ሰዎች ተዘጋጅተው ሲጠብቁ እንደነበርና እነዚህ ሃይሎች ጥቃቱን እንደፈጸሙት የአካባቢው ነዋሪዎች ተናግረዋል።
ጥቃቱ እንደተፈጸመ የእሳት አደጋ መኪና የደረሰ ቢሆንም፣ ቃጠሎውን መቆጣጠር ሳይችል ቀርቷል። የአጋዚ ወታደሮች አካባቢውን በመቆጣጠራቸው መኪናውን ምን እንደጫነ ለማወቅ ሳይችሉ መቅረታቸውንም ነዋሪዎች ገልጸዋል።
በጎንደር እና ትግራይ መካከል በደባርቅ በኩል የሚደረገው የትራንስፖርት እንቅስቃሴ መንገዱ አደጋኛ በመሆኑ እንዲቋረጥ ተደርጓል። በሁመራ በኩል የሚደረገው ጉዞ እንዳማራጭ ጥቅም ላይ እየዋለ ባለበት ወቅት፣ የአሁኑ ጥቃት ይህንንም መንገድ ለተሽከርካሪ ዝግ ያደርገዋል የሚል ግምት አሳድሯል። በአካባቢው የሚንቀሳቀሱ የነጻነት ሃይሎች የሚፈጽሙት የደፈጣ ጥቃት መጨመር አገዛዙ በአካባቢው ያለውን ወታደራዊ ሃይሉን እንዲጨምር አስገድዶታል።
በወለቃ ላይ ለተፈጸመው ጥቃት እስካሁን ድረስ ሃላፊነቱን የወሰደ ሃይል የለም።