በኢትዮጵያ የሚታየው የዘይት እጥረት እንደቀጠለ ነው

ሰኔ ፲፫( አሥራ ሦስት ) ቀን ፳፻፱ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- 11 በመቶ እድገት መገኘቱ በየጊዜው በሚነገርባት ኢትዮጵያ የዘይትና የስኳር እጥረት ለአመታት ዋና ተፈላጊ የምግብ ሸቀጦች ሆነው ቀጥለዋል።
በዋና ከተማዋ ዜጎች ዘይት ለማግኘት ሌለቱን በሰልፍ ያሳልፋሉ። ዘይት አከፋፋይ ድርጅቶች ዜጎች በሌሊት እንዳይሰለፉ ማስታወቂያዎችን እስከመለጠፍ ቢደርሱም፣ ወረፋው አልቀነሰም።
አንድነት የሸማቾች ማህበር ግንቦት 24 ቀን 2009 ዓም ባወጣው ማስታወቂያ “ አገልግሎት የሚሰጡ ሰራተኞች የስራ ሰአት መግቢያ 2 ሰአት ሆኖ እያለ፣ ያለ ሰአቱ በሌሊት መጥተው የሚሰለፉ ተገልጋዮች ከህግ ውጭ በመሆኑ፣ ከእንግዲህ በሌሊት የሚሰለፉትን በህግ የምናስጠይቅ መሆኑን እንገልፃለን “ የሚል ማስታወቂያ አውጥቷል።
የዘይት ወረፋ በመጠበቅ አብዛኛውን የስራ ጊዜያችንን እናጠፋለን የሚሉት ተገልጋዮች፣ ችግሩ ከአመት አመት ይቀረፋል ቢባልም አለመሻሻሉን ይናገራሉ።