በቤት ውስጥ የመቀመጥ አድማ በመላው ኦሮሚያ ዛሬ ተጀመረ

(ኢሳት ዜና –ነሐሴ 17/2009) ለ5 ቀናት የተጠራው በቤት ውስጥ የመቀመጥ አድማ በመላው ኦሮሚያ ዛሬ ተጀመረ።

ከሀረር እስከ ጉደር፡ ከባሌ እስከ እስከ ሰላሌ፡ ሰበታ፡ ሆለታ፡ መላው የሀረርጌ ከተሞች፡ አዲስ አበባ ዙሪያ፡ አምቦ፡ ነቀምት፡ በሁሉም የኦሮሚያ አቅጣጫዎች አድማው በይፋ ተጀምሯል። ንግድ ቤቶች ሙሉ በሙሉ ተዘግተዋል።
የትራንስፖርት አገልግሎት ተቋርጧል። መንገዶች ላይ የሚታዩት ታጣቂዎች ናቸው። በአንዳንድ አከባቢዎች የወጣቶቹን ጥሪ ወደ ጎን አድርገው ሲንቀሳቀሱ በነበሩ ተሽከርካሪዎች ላይ ጥቃት መሰንዘሩ ታውቋል።
ከተለያዩ የኢትዮጵያ አካባቢዎች ወደ ኦሮሚያ ክልል የህዝብ ማመላለሺያ አውቶብሶች መግባት ሳይችሉ በያሉበት መቆማቸውንም የደረሰን መረጃ አመልክቷል።

በጅማ ዞን ሊሙ ሆሳ ወረዳ ደግሞ የወ/ሮ አዜብ መስፍን ንብረት የሆነ ከ200 ሄክታር መሬት ላይ የተለቀመ ቡናን የአካባቢው ነዋሪዎች ተከፋፍለውታል።
አድማውን የጠሩት የኦሮሞ ወጣቶች ቄሮዎች ናቸው። ከአንድ ሳምንት በፊት ጀምሮ ለአምስት ቀናት የሚቆይ አድማ እንደሚደረግና ማንኛውም አይነት እንቅስቃሴ እንደሚቆም በመግለጽ ጥሪው ከተላለፈበት ጊዜ ጀምሮ በአብዛኛው የኦሮሚያ አከባቢዎች ውጥረት ነግሶ ነበር የሰነበተው።
አድማው ረቡእ ይጀመራል ተብሎ የተገለጸ ቢሆንም ከዋዜማው አንስቶ የተሽከርካሪዎች እንቅስቃሴ መገደቡ የአድማውን አይቀሬነት ያረጋገጠ ነበረ።

በተለያዩ ከተሞች የህዝብ ማመላለሺያ አውቶቡሶች ከዋዜማው አንስቶ መንቀሳቀስ ያልቻሉ ሲሆን በመናሃሪያዎች ተጨናነቀው እንደነበረም መዘገቡ ይታወሳል። ዛሬ በተለይ በምስራቅና ምዕራብ ሀረርጌ ከማለዳው ጀምሮ ከእንቅስቃሴ ውጪ በመሆን አድማውን በይፋ ሲጀምሩት፡ በሌሎች የኦሮሚያ ከተሞች ቀስ በቀስ ተቀላቅለውት ከቀትር በኋላ ሙሉ በሙሉ በሚባል መልኩ አድማው መካሄዱን ነው ከየአካባቢው ለኢሳት የደረሱት መረጃዎች ያረጋገጡት።

የምዕራብ ሀረርጌዋ አሰቦት ከቤት ውስጥ ያለመውጣት አድማውን የጀመረችው ንጋት ላይ ነው። ሱቆች እንደተዘጉ ናቸው። የተከፈተ የንግድ ቦታ የለም። መንገዶች ከእንቅስቃሴ ውጭ በመሆናቸው የተወረረ ከተማ ይመስል ነበር ብለዋል ያነጋገርናቸው። ሰዉ ከቤት አልወጣም። ፖሊሶችና እንስሳት ብቻ መንገድ ላይ ይታያሉ።
እስካሁን ባለው መረጃ አድማው በወለጋ፣ ጊምቢ፣ ሆለታ፣ ሃሮማያ፣ አወዳይ፣ ደምቢ ዶሎ፣ ባሌ ሮቤ፣ ጭሮ፣ ሻሸመኔ፣ አምቦ፣ ቡራዩ፣ ሆለታ፣ ባኮ፣ ግንደበረትና በመሳሰሉት ከተሞች ተጠናክሮ ቀጥሏል።
ከአዲስ አበባ ተነስተው ጉዞቸውን ወደ ሃረር፣ ድሬዳዋ፣ ጅጅጋ፣ ሚዛን ተፈሪ ፣ ጋምቤላ እና ኦሮምያ ክልልን አቋርጠው ወደተለያዩ ክልሎች የሚሄዱ ሰላም ፣ ጎልደን እና ፋልኮን የሚባሉ አውቶቡሶች ጉዞአቸውን ሰርዘዋል።

የተሽከርካሪ ባለቤቶች በመኪኖቻቸው ላይ ለሚደርሰው ጉዳት መንግስት እንደማይሸፍንላቸውና ሁኔታው ካልተረጋጋ በስተቀር እንደማይጓዙ ለመንገደኞች ገልጸዋል።
ከአዲስ አበባ ወደ አምቦ፡ ነቀምት፡ አዳማና ሌሎች ከተሞች የሚጓዙ ተሽከርካሪዎች ዛሬ ሙሉ በሙሉ ተገተዋል። ከአዲስ አበባ ወደ ምዕራቡ የኢትዮጵያ ክፍል ወሊሶን ጨምሮ የሚደረገው ጉዞ አደገኛ በመሆኑ ተሸከርካሪዎች ዝር ሳይሉ መዋላቸው ታውቋል።

ዛሬ ከሀዋሳ ወደ አዲስ አበባ ጉዞ ለማደረግ ትኬት የቆረጡ መንገደኞች መናሃሪያ ቢሄዱም የሚሳፈሩባቸው አውቶብሶች ጥቃት ይደርስብናል በሚል ፍራቻ እንደማይንቀሳቀሱ ተነግሯቸው ወደየቤታቸው መመለሳቸውንም የደረሰን ዜና ያመለክታል።
በሻሸመኔ መስመር እስከ አዲስ አበባ ባለው መንገድ በተለይም በአርሲ ነጌሌ፣ ዝዋይ፣ መቂ አካባቢ ምንም ዓይነት የትራንስፖርት እንቅስቃሴ እንደሌለም ታውቋል። ዛሬ በኮፈሌ የሚቆመው ትልቁ ገበያ በሰው ድርቅ ተመቶ የዋለ ሲሆን የመንግስት ታጣቂዎች በአካባቢው ያገኙዋቸውን ወጣቶች አፍሰው እንደወሰዷቸው ተመልክቷል።
ጅጅጋ አካባቢ ተነስቶ ወደ አዲስ አበባ ይጓዝ የነበረ የህዝብ ማመላለሻ አውቶቡስ ባቢሌ አካባቢ ችግር በመኖሩ ሲመለስ፣ ሃረር አራተኛ እየተባለ በሚመጠራው አካባቢ ደግሞ የህወሃት ንብረት የሆነው ሰላም ባስ በድንጋይ ተሰባብሯል።

በአዲስ አበባ ዙሪያ ያሉ የኦሮሚያ ከተሞች አድማውን መቀላቀላቸውም ተሰምቷል። የባለፈው ተቃውሞ የተጋጋለባት ሰበታ ዛሬም አድማውን በይፋ ጀምራለች። ቡራዩም በተመሳሳይ ሱቆችና መደብሮች ተዘግተው ነው የዋሉት።
አስጎሪና ሆለታ በአድማው ጠንካራ እንቅስቃሴ ከተደረገባቸው አከባቢዎች የሚጠቀሱ ሲሆን በተለይ በሆለታ አንድ የመንገደኞች አውቶብስ ላይ ጥቃት ተሰንዝሮበታል። በወለጋም አድማው በስፋት የተካሄደ ሲሆን ነቀምት ጭር ብላ ውላለች። በአጠቃላይ በኦሮሚያ የተመታው አድማ የተሳካ ነው ይላሉ ያነጋገርናቸው።

ለህዝባዊ ወያኔ ሀርነት ትግራይ መንግስትም ሆነ ለክልሉ የኦህዴድ ቡድን የዛሬው አድማ ከፍተኛ ኪሳራ ሆኖ ተመዝግቧል።በተለይም ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የኦሮሞን ህዝብ ስነልቦና ለማሸነፍ የተለያዩ ፖለቲካዊ እርምጃዎችን እየወሰድኩ ነው ለሚለው ኦህዴድ ትልቅ ሽንፈት ተደርጎ ተቆጥሯል።

የኢኮኖሚ አብዮት በኦሮሚያ ተጀምሯል፡ በሚል ዳግም ተቃውሞ እንደማይነሳ ገልጸው አዲስ አመራር በመሰየም የኦሮሞን ህዝብ ትግል እናዳክማለን ብለው ለተነሱት የህወሃትና የኦህዴድ ባለስልጣናት ዛሬ ግልጽ መልዕክት እንዲደርሳቸው ተደርጓል ሲሉ ታዛቢዎች ይናገራሉ። የኦሮሞ ወጣቶች ለ5 ቀናት የተጠራው አድማ ይቀጥላል፡ ሌላው የኢትዮጵያ ህዝብ እንዲቀላቀል ጥሪ አድርገዋል።