በባህርዳር በሚካሄድ የቤት ማፍረስ ዘመቻ በሺዎች የሚቆጠሩ ዜጎች መጠለያ አልባ ሆኑ

መጋቢት ፲፬ (አሥራ አራት)ቀን ፪፲፻፱ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- ነዋሪዎች ለኢሳት እንደገለጹት ያለምንም ተለዋጭ ቤትና ቦታ ከመኖሪያቸው እንዲፈናቀሉ የተደረጉት፣ በቀበሌ 14 አካባቢ የሚኖሩ ዜጎች ለከፍተኛ ችግር ተዳርገዋል። ትናንት ባሉዋን ሲደበድቡባት ጩኸት ያሰማች ነፍሰጡር ሴት ፣ በፖሊሶች በደረሰባት ድብደባ ከፉኛ ተጎድታ ሆስፒታል ገብታለች። አንድ ህጻንም በነበረው ግርግር ተረጋግጣ ህይወታ ማለፉ ታውቋል።
አብዛኞቹ ወጣቶች ጫካ በመግባት ከድብደባ አምልጠዋል። ሁኔታው አስከፊ መሆኑን የሚናገሩት ነዋሪዎች፣ በአገራችን የት እንሂድ ሲሉ ይጠይቃሉ። በርካታ ጉዳት የደረሰባቸው ሰዎች፣ የሚመለከታቸው ሁሉ ፈጥነው እንዲደርሱላቸው ጥሪ አቅርበዋል።
በአካባቢው በተለያዩ አመታት ተስረተው የነበሩ ወደ 2 ሺ የሚጠጉ ቤቶች እንሚፈርሱ ነዋሪዎች ገልጸዋል።
ይህ በእንዲህ እንዳለ በዚሁ አካባቢ ይኖር የነበረ የዙሪያ ወረዳ የጸጥታ ዘርፍ ሃላፊ የሆነው የወታደር ባህሩ ቤት ሌሊት ላይ ማንነታቸው ባልታወቁ ሃይሎች በቦንብ መምታቱ ታውቋል። ጥቃቱ በቤተሰቦቹ ላይ ያደረሰው የህይወት ጉዳት ባይኖርም፣ በቤቱ ላይ ግን ጉዳት አድርሷል።