በሞጆ የሚገኙ የጨርቃጨርቅ ፋብሪካዎች በኤሌክትሪክ መቋረጥ ሳቢያ ከቅዳሜ ጀምሮ ምርት ማቆማቸው ተገለጸ

ኢሳት (የካቲት 14 ፥ 2009)

በሞጆ የሚገኙ የጨርቃጨርቅና ሌሎች ፋብሪካዎች በኤሌክትሪክ መቋረጥ ሳቢያ ከቅዳሜ ጀምሮ ምርት ማቆማቸው ታወቀ።

የሞጆ ቆዳ ማምረቻ፣ ጆርጅ ጫማ የተሰኘና ምርቶቹን ለውጭ ሃገር ገበያ የሚያቀርብ ፋብሪካ፣ የኢትዮ-ጃፓን የጨርቃ-ጨርቅ ፋብሪካዎች፣ አዲስ ሞጆ የምግብ ዘይት ኮምፕሌክስና የሞጆ ደረቅ ወደብ ምርት ካቆሙ ፋብሪካዎች መካከል ዋና ዋናዎቹ መሆናቸው ተመልክቷል።

ፋብሪካዎቹ ምርት በማቆማቸው ምክንያት የምርት መስተጓጎልና በትዕዛዝ መድረስ የነበረባቸው ምርቶች ሊደርሱ አለመቻላቸውን የፋብሪካዎቹ ሃላፊዎች አስታወቀዋል።

የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት በበኩሉ በኤሌክትሪክ መሳሪያ (ብሬከር) ላይ በደረሰ የብልሽት አደጋ ከተማዋ ከቅዳሜ ጀምሮ  የኤሌክትሪክ አገግሎት ማጣቷንና ችግሩ በከተማዋ በሚገኙ ፋብሪካዎች ላይ ተፅዕኖ ማሳደሩን ለመንግስት መገናኛ ብዙሃን ገልጸዋል።

በፋብሪካዎቹና በወደቡ የሚሰጡ አገልግሎቶች እንዲቀጥሉ ለማድረግ መስሪያ ቤቱ ከፍተኛ ጥረትን እያደረገ እንደሚገኝ የመስሪያ ቤቱ የኮሚዩኒኬሽን ዳይሬክተር አቶ ገብረእግዚያብሄር ታፈረ ተናግረዋል።

አጋጥሟል የተባለውን ይህንኑ ችግር በቀጣዮቹ ሁለት ቀናቶች እልባት ለመስጠት ባለሙያዎች ርብርብ እያደረጉ መሆኑን ሃላፊው አክለው ገልጸዋል።

በከተማዋ ያሉ ፋብሪካዎች በበኩላቸው በትንሹ ለአምስት ቀናቶች ምርት ሳያመርቱ መቆየታቸው ለከፍተኛ ኪሳራ እንደሚዳርጋቸው በመግለጽ ላይ ናቸው።

በሃገሪቱ እያጋጠመ ያለው ተደጋጋሚ የኤሌክትሪክ ሃይል መቆራረጥና ብልሽት በኢትዮጵያ የውጭ ንግድ እንቅስቃሴ ላይ ከፍተኛ ተፅዕኖ በማሳደር ላይ መሆኑን የኢንዱስትሪ ሚኒስቴር ሲገልጽ መቆየቱ ይታወሳል።

አዲስ አበባ ከተማን ጨምሮ በተለያዩ ክልሎች የሚገኙ ነዋሪዎችና የንግድ ተቋማት በዚሁ የኤሌክትሪክ መቆራረጥ ሳቢያ የዕለት ከዕለት እንቅስቃሴያቸው ለችግር መዳረጉን ይገልጻሉ።

የመንግስት ባለስልታናት ችግሩ በአጭር ጊዜ ውስጥ እልባትን ያገኛል ሲሉ በተደጋጋሚ ቃል ቢገቡም የኤሌክትሪክ ሃይል መቆራረጡ ለአመታት እልባት ሳያገኝ መቀጠሉን ነዋሪዎች አስታወቀዋል።