በመንግስትና በኦሞ ሸለቆ በሚኖሩ ኢትዮጵያውያን መካከል ያለው ውዝግብ እንደቀጠለ ነው

ጥር 5 ቀን 2004 ዓ/ም

ት ዜና:-መንግስት በአካባቢው የሚኖሩ በርካታ ብሄረሰቦችን በማፈናቀል ፣ መሬታቸውን ለእርሻ ልማት ማዋሉ የአካባቢውን ነዋሪዎች ማስቆጣቱን ለአዲሲቷ ኢትዮጵያ የጋራ ንቅናቄ አስታውቋል።

ንቅናቄው የቦዲ ብሄረሰብ አባላት በጭነት መኪና ቀያቸውን ለቀው ከተጋዙ በኋላ በመሬታቸው ላይ ስላላቸው መብት መንግስት እንክብካቤ እንዲደረግላቸው ቢጠይቁም ምላሽ አላገኙም።

ታህሳስ 28፣ 2004ዓም ወ/ሮ ቢኮሉ የተባሉ ሴት ወደ ከብቶቻቸው እየተጓዙ ባለበት ወቅት በከባድ ጭነት መኪና ተገጭተው መሞታቸውን፣  የቀብር ስነሥርዓታቸው ከተከናወነ በኋላ ቤተሰቦቻቸው ሁኔታው እንዲጣራና አስፈላጊም የሆነው ካሣ ከፍትሕ ጋር እንዲሠጣቸው ቢጠይቁም ከመንግሥት የተሰጣቸው ምላሽ ማስፈራራትና ዛቻ እንደሆነ ገልጧል።

 እንዲያውም የአካባቢው የመንግሥት ተወካይ የሟች ባለቤት እጃቸውን ለመንግሥት መስጠት እንዳለባቸውና እየፈጠሩ ላለው ችግር ወደ እስር ቤት መወሰድ እንዳለባቸው ፣ ግለሰቡ በፈቃዳቸው እጃቸውን የማይሰጡ ከሆነ ‹‹እሳቱን ወደ እነርሱ›› እንደሚያመጡት ባለሥልጣኑ በእብሪት መናገራቸውን ንቅናቄው አክሎ ገልጧል፡፡

የንቅናቄው ዋና ዳይሬክትር የሆኑት አቶ ኦባንግ ሜቶ ለኢሳት ሲናገሩ፣ በአሁኑ ጊዜ ችግሩ እየተካረረ በመምጣቱ፣  በሳምንቱ ውስጥ  ሁለት ሰዎች ተገድለዋል።