የኦብነግ አመራር አባልን የሶማሊያ መንግስት አሳልፎ መስጠቱ ዓለም አቀፍ ሕግን የሚጻረር ነው ተባለ

(ኢሳት ዜና–ጳጉሜ 3/2009) የኦጋዴን ብሔራዊ ነጻነት ግንባር /ኦብነግ/አመራር አባል አብዲካሪን ሼህ ሙሴን የሶማሊያ መንግስት አሳልፎ መስጠቱ ዓለም አቀፍ ሕግን የሚጻረር ነው ሲል አፍሪካ ራይትስ ሞኒተር አወገዘ።

በጄኔቫ አውሮፓ የሚገኘው አፍሪካ ራይትስ ሞኒተር ጉዳዩን አስመልክቶ ባወጣው መግለጫ የኦብነጉ መሪ ያለፍላጎታቸው ለኢትዮጵያ ተላልፈው መሰጠታቸው እንደ አውሮፓውያኑ አቆጣጠር በ1954 የወጣውን የተባበሩት መንግስታት ስምምነት የሚጣረስ ነው።

አፍሪካን ራይትስ ሞኒተር በመግለጫው እንዳመለከተው የኢትዮጵያው አገዛዝ የሰዎች ነጻነት የሚያከብርና ለፍትህ የቆመ ስርአት አይደለም እናም ማንኛውም ስደተኛም ሆነ የፖለቲካ ተቀናቃኝ ለኢትዮጵያ ተላልፎ ሲሰጥ ሰቆቃና ግድያ ሊደርስበት ይችላል ሲል ስጋቱን ገልጿል።

የኦብነጉ መሪ አብዲካሪን ሼህ ሙሴም በሶማሊያ መንግስት ይሁንታ ለኢትዮጵያ ተላልፎ መሰጠቱ ለሰቆቃ ወይም ግድያ ሊዳርገው እንደሚችል አፍሪካ ራይትስ ሞኒተር ባወጣው መግለጫ አስታውቋል።

እንደ ተቋሙ ገለጻ የኦብነጉ መሪ ለኢትዮጵያ ተላልፎ መሰጠት እንደ አውሮፓውያኑ አቆጣጠር በ1954 የወጣውን የተባበሩት መንግስታት ስምምነት የሚጻረር ነው።

ይህ ሆኖ እያለ የሶማሊያ ማስታወቂያ ሚኒስቴር ሰውየው ተላልፎ የተሰጠው ከኢትዮጵያ ጋር በተደረገው የጸረ ሽብር ስምምነት ነው ማለቱ እጅግ የሚያሳስብ ነው ብሏል።

በሶማሊያ የአፍሪካ ሰላም አስከባሪ ሃይል/አሜሶም/ጥላ ስር ያሉ የኢትዮጵያ ወታደሮች በሐገሪቱ ሚስጥራዊ ቡድኖችን በማቋቋም ሐገሪቱን በእጅ አዙር እያመሱ ይገኛሉ።

የኦብነጉ መሪ አብዲካሪን ሼህ ሙሴም የታገቱት በዚሁ መንገድ መሆኑ ተገልጿል።

የሶማሊያ መንግስት በደነገገው ህገ መንግስት መሰረት ማንኛውም የሀገሪቱ ዜጋ መብቱ ተጠብቆ ደህንነቱ ሊረጋገጥ ይገባል።እናም በፋርማጆ የሚመራው የሶማሊያ መንግስት ሰብአዊ መብቶችን እንዲያከብር አፍሪካ ራይትስ ሞኒተር ጠይቋል።

በተለይም የስደተኞችን ደህንነት በተመልከተ አለም አቀፍ ህግን መሰረት አድርጎ ሊሰራ ይገባል ብሏል። አፍሪካ ራይትስ ሞኒተር።