ወደ ስድስት መቶ የሚሆኑ ሶማሊያውያን የተገደሉበት አንደኛ ዓመት ሢታሰብ ተከሳሹ በአደባባይ እንዲወገድ ተደረገ።
በአዲስ አበባና በሶማሊያ ከአርባ ዓመት በኋላ በረራ የተጀመረ ሲሆን፣ በዕለቱ አልሸባብ ጥቃት ፈጽሟል።
( ኢሳት ዜና ጥቅምት 05 ቀን 2011 ዓ/ም ) በሶማሊያ ታሪክ አሰቃቂውን የቦምብ ፍንዳታ በመፈጸም ስድስት መቶ ለሚጠጉ ሰላማውያን ዜጎች ሞት ምክንያት የሆነው ሀሰን አዳን ይስሀቅ ትናንት የሟቾቹ አንደኛ ዓመት ሲከበር በአደባባይ እንዲወገድ ተደርጓል።
ሀሰን አዳን ልክ የዛሬ ዓመት ነበር ከፍተኛ ተቀጣጣይ ቦምብ የተጠመደበት የኪራይ የጭነት መኪና እያሽከረከረ ሰው ወደሚበዛበት የሞቃዲሾ ጎዳና በመግባት ፍንዳታውን የፈጸመው።
ጥቃቱን አስመልክቶ እስካሁን ኃላፊነቱን የወሰደ ቡድን ባይኖርም፣ ሀሰን አዳን ቀደም ሲል የአልሸባብ ሚሊሻዎች መሪ ከመሆኑ አኳያ ከጥቃቱ ጀርባ ቡድኑ ሳይኖር እንደማይቀር ይታመናል።
በፍንዳታው ውዶቻቸውን ካጡት ሶማሊያውያን መካከል የስድስት ህጻናት ልጆች እናት የሆነችው ፎዊሳ ሳላህ ኡስማን አንዷ ነች። የፎይሳ ባለቤት ወይም የስድስቱ ህጻናት አባት አስከሬን እንደሌሎቹ ሰለባዎች ሁሉ አልተገኘም።በከፍተኛው ፍንዳታ ወደ ፍርስራሽነት ተቀይሯል።
ፎይሳ ውዷን ካጣች ዓመት ቢቆጠርም፣ መጽናናትን እምቢ አንዳለች ነው። ትናንት በመኖሪያ ቤቷ ተገኝተው ላነጋገሯት የቢቢሲ ጋዜጠኞች፦“አሁንም በጥልቅ ሀዘን ላይ ነኝ።ልቤ እንደተሰበረ ነው።ምንም ነገር መሥራት አልችልም” ስትል እያለቀሰች ተናግራለች።
የተከሳሽ ሀሰን አዳን ይስሀቅን ጉዳይ ሲከታተል የነበረው ፍርድ ቤት ባሳለፈው ውሳኔ መሰረትም፣ ተከሳሹ በትናንትናው ዕለት -የገደላቸው ሰላማውያን የሙት ዓመታቸው ሲከበር እዚያው እነሱን በገደለበት ጎዳና በአደባባይ ተገድሏል።.
ሟቾቹን ለማስታወስ ሲባልም ጎዳናው “ ጥቅምት 14 አደባባይ” ተብሎ ተሰይሟል። ይህ በእንዲህ እንዳለ ቅዳሜ ምሽት ላይ ሁለት አጥፍቶ ጠፊዎች በባይደዋ ከተማ በፈጸሙት ጥቃት ሀያ ሰዎች ሲገደሉ በርካቶች ቆስለዋል።
አልሸባብ የተሰኘው ቡድን ለጥቃቱ ኃላፊነቱን እንደሚወስድ አስታውቋል። እንደ ቢቢሲ ዘገባ፣ ከ41 ዓመት በኋላ በአዲስ አበባና በሞቃዲሾ መካከል ለመጀመሪያ ጊዜ የንግድ አውሮፕላን በረራ የተጀመረው በዚሁ ጥቃቱ በተፈጸመበት ዕለት ነው።.
በኢትዮጵያ የግል አየር መንገድ ንብረት የሆነ አውሮፕላን ቅዳሜ ዕለት በሶማሊያው -“አደን አዴ አውሮፕላን ማረፊያ” የደረሰ ሲሆን፣ ይሕ ከአርባ አንድ ዓመት በኋላ የተጀመረው በረራ-አየር መንገዱ በሳምንት አራት ጊዜ ለመብረር ለያዘው ዕቅድም- የመጀመሪያው ጉዞ ነው።
ይህም በሁለቱ የምሥራቅ አፍሪካ ጎረቤት ሀገራት መካከል ግንኙነቶች እየተሻሻሉ ለመምጣታቸው ተጨማሪ ምልክት ነው ተብሏል።