ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ የክብር ተናጋሪ ሆነው እንዲቀርቡ ተጠየቀ

(ኢሳት ዲሲ–ሐምሌ 27/2010) ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የክብር ተናጋሪ ሆነው እንዲቀርቡ ተጠየቀ።

በመንግስታቱ ድርጅት የስዊዲን አምባሳደር ኦሎፍ እስኩግ በጸጥታው ምክር ቤት ስብሰባ ላይ  ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ በኢትዮጵያና በኤርትራ መካከል ሰላም መፍጠር የቻሉ መሪ በመሆናቸው በምክር ቤቱ የክብር ተናጋሪ እንዲሆን መጠየቃቸውን ለማወቅ ተችሏል።

ተስፋ የቆረጥንበትን የሁለቱን ሀገራት ፍጥጫ በአጭር ጊዜ መፍትሄ የሰጡ መሪ በማለትም አምባሳደሩ አድናቆታቸውን ገልጸዋል።

በሌላ በኩልም አንድ የስዊዲን ፓርላማ አባል ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድን ለኖቬል ሽልማት እጩ ለማድረግ ዘመቻ መጀመራቸውን የደረሰን ዜና ያመለክታል።

በመንግስታቱ ድርጅት የስዊዲን አምባሳደር ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ በኢትዮጵያና ኤርትራ መሀል ሰላም እንዲሰፍን ለወስዱት ቁርጠኛ እርምጃ አድናቆት የሰጡት ትላንት ትላንት ነው።

የጸጥታው ምክር ቤት አባላት በትሰበሰቡት መድረክ ላይ ጉዳዩን ያነሱት አምባሳደር ኦሎፍ እስኩግ እኛ ሞክረን ያልተሳክውን እሳቸው ውጤታማ አደረጉት በማለት ምስክረነታቸውን ሰጥተዋል።

እስከአሁን ያድረግነው ጥረት  ውጤታማ ባለመሆኑ ተስፋ የቆረጥንበትን የ20 ዓመቱን የኢትዮጵያና የኤርትራ ጉዳይ ቆራጥ እርምጃ በመውሰድ ታሪካዊ ሆነው ብቅ ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ በጠቅላላ ጉባዔው የክብር ተናጋሪነት ስፍራ ሊሰጣቸው አይገባምን? ሲሉ የምክር ቤቱ አባላትን ጠይቀዋል።

ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አስቸጋሪ ሁኔታዎችን ወደ ሰላም በመቀየር እኛ ውጤታ ያጣንበትን ጥረት መፍትሄ ያስገኙ መሪ በመሆናቸው በመንግስታቱ ድርጅት ጠቅላላ ጉባዔ ላይ ተገኝተው የክብር ተናጋሪ እንዲሆኑ መደረግ አለበት ሲሉ ተናግረዋል።

አምባሳደር እስኩግ እንዳሉት ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ በጠቅላላ ጉባዔ ላይ የክብር ተናጋሪ ሆነው የወሰዱትን እርምጃ በተመለከተ ሌሎች መሪዎች እንዲሰሙት መደረግ ይኖርበታል።

ጠቅላይ ሚኒስትሩ ያን ውሳኔ ለምን ለመውሰድ ፈለጉ? ውሳኔው ለሀገራቸው ምን ማለት ነው? ለሚሉት ጥያቄዎች መልስ ሊሰጡን ይችላሉ ብለዋል አምባሳደሩ።

እሳቸው የተከተሉት ተምሳሌታዊ አካሄድ ሌሎች ሀገራት ከጎረቤቶቻቸው ጋር ስለሚኖራቸው ግንኙነት አርዓያ እንደሚሆን የጠቆሙት አምባሳደር እስኩግ በገንዘብ በዲፕሎማሲውና በወታደራዊ በኩል የሚወጣውን መዋዕለ ነዋይ እንደዚህ ዓይነት ሰላማዊ መፍትሄዎችን ለማምጣት ለሚደረግ ጥረት ብናውለው የተሻለ እንደሆነ ያመላከትን ነው ብለዋል።

በመሆኑም የመንግስታቱ ድርጅት ጠቅላላ ጉባዔ በመጪው የመሪዎች ስብሰባው ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድን የክብር ተናጋሪነት ስፍራ እንዲሰጣቸው ጠይቀዋል።

በተያያዘ ዜናም የስዊዲን የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባል ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድን ለኖቤል የሰላም ሽልማት እጩ እንዲሆኑ መጠቆማቸው ታውቋል።

የምክር ቤት አባሉ አንድሬስ ኦስተርበርግ ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ ባለፉት ሶስት ወራት የወሰዷቸው ታሪካዊ እርምጃዎች ለሰላም የኖቤል ሽልማት የሚያበቃቸው መሆናቸውን በመጥቀስ እጩ እንዲሆኑ ለማድረግ ጥረት መጀመራቸውን ያገኘነው መረጃ ያመልክታል።

የአሜሪካው ከፍተኛ ዲፕሎማት ሀርማን ኮሆን ለመጀመሪያ ጊዜ ለኖቤል ሽልማት የማጨው ሰው አገኘሁ ብለው ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድን መጥቀሳቸው የሚታወስ ነው።