ግንቦት 7 ጅሐዳዊ ሐረካት ተብሎ የተዘጋጀውን ፊልም አወገዘ

ጥር ፴ (ሰላሳ) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም

ኢሳት ዜና:-ግንቦት ሰባት የፍትህ የነጻነትና የዲሞክራሲ ንቅናቄ ለኢሳት በላከው መግለጫ ጅሃዳዊሐረካት የተባለው ድራማ ሁለቱን ትልልቅና ጥንታዊ የኢትዮጵያ ሐይማኖቶች ለማጣላት ሆን ተብሎ የተሰራ ነው ብሎአል።

ኢትዮጵያ እስልምናንም ሆነ ክርስትናን በቅድምያ ከተቀበሉ አገሮች አንዷ መሆኗ ብቻ ሳይሆን ክርስትናና እስልምና ከአንድ ሺ አመታት በላይ በሠላም ተከባብረዉ ጎን ለጎን የኖሩባት ብቸኛ አገር መሆኑዋን የገለጠው ግንባሩ፣ የአገር አንድነትና የህዝብ ሠላም እረፍት የሚነሳዉ አገዛዙ ግን ይህንን ዘመናት ያስቆጠረ ታሪክ ለመለወጥና የህዝብን በሠላም አብሮ መኖር ለማደፍረስ ቆርጦ የተነሳ ይመስላል ብሎአል።

የኢትዮጵያ ህዝብ አኬልደማን አይቶ ትግሉን አጠናክሮ እንደቀጠለ የገለጠው ግንቦት7፣ ጅሃዳዊ ሐረካትን አይቶ የጀመረዉን ትግል ከፍጻሜዉ ለማድረስ በተጠንቀቅ እንዲቆም ጥሪ አድርጓል።

ይህ በእንዲህ እንዳለ በእስር ላይ የሚገኙ የድምጻችን ይሰማ ኮሚቴ አባላት ሰብሳቢ የሆኑት ኡስታዝ አቡበክር ለፍርድ ቤት እንደተናገሩት ማእከላዊ እስር ቤት ላይ በነበሩበት ጊዜ የተፈጸመባቸውን ግፍ ዘርዝረው አቅርበዋል። በእስረኞች ላይ የደረሰው በደል አልበቃ ብሎ የሀሰት ምስክሮች ቀርበው እንዲመሰክሩ መደረጉን፣ በመቀጠልም ኢቲቪ በአደባባይ ፍርድ ቤቱ ወንጀለኛ ሳይላቸው፣ ወንጀለኛ አድርጎ እንዳቀረባቸው ለፍርድቤቱ ገልጸዋል። ውሳኔው በኢቲቪ አስቀድሞ የተሰጠ በመሆኑም ፍርድ ቤቱ ከዚህ በሁዋላ መሰየሙ ትርጉም እንደሌለው ሰብሳቢው ተናግረዋል። ዳኞቹ ፊልሙ እንዳይተላለፍ የሰጡት ትእዛዝ በምን ሁኔታ ሳይተገበር እንደቀረ ለእስረኞች ገልጸዋል፣ ይሁን እንጅ ፊልሙ በፍርድ ቤቱ ሂደት ላይ የሚያመጣው ተጽእኖ እንደሌለም ገልጸውላቸዋል።

ስማቸው እንዳይጠቀስ የፈለጉ የህግ ባለሙያ፣ ” ኢቲቪ ያስተላለፈው ፊልም  አንድ ሰው ከፍርድ ውሳኔ በፊት ነፃ ተብሎ የመገመት መብቱን ማሳጣት ብቻ ሳይሆን፤ በችሎቱ ላይ የተቀመጡት ዳኞች የይስሙላ መሆናቸውን ለማሳየት እና እስረኞቹ የሚያደርጉትን ክርክር ዋጋ ለማሳጣት” ነው ብለዋል።

ይህ በእንዲህ እንዳለ ሙስሊም ኢትዮጵያውያን በነገው እለት ከፍተኛ ተቃውሞ እንደሚያሰሙ ከተላለፈው መርሀ ግብር ለመረዳት ተችሎአል።