ግንቦት 7 የፍትህ የነጻነትና የዲሞክራሲ ንቅናቄ ከ ጥር 12 ቀን ጀምሮ ሶስተኛ አመታዊ ጉባኤውን በተሳካ ሁኔታ ማካሄዱን ገለጠ

ጥር 20 ቀን 2004 ዓ/ም

ኢሳት ዜና:-የንቅናቄው የህዝብ ግንኙነት ክፍል ለኢሳት በላከው መግለጫ እንደገለጠው በጉባኤው ኢትዮጵያ ውስጥ ያሉ የክልል ተወካዮችን ጨምሮ የአውሮጳ፤ የአፍሪካ፤ የኦሲኒያ፤ የመካከለኛው ምስራቅ፤ የካናዳ፤ የሰሜን አሜሪካና የአውሮጳ ተወካዮች እየተሳተፉበት ነው።

በዚህ ሶስተኛ ጉባኤ ላይ በዋንኛነት መነጋገሪያ አጀንዳ የሆነው ከወያኔ ጋር እየተካሄደ ያለው የጸረ ዘረኝነት ትግል ይበልጥ ተጠናክሮ በአጭር ጊዜ ውስጥ ግቡን ሊመታ የሚችልበትን ድርጅታዊ አቅም በማጎልበት ላይ የሚያተኩር ነው።

የንቅናቄው ጉባኤ እስከዛሬ ባካሄደው ስብሰባ አዲሱን የድርጅቱ የትግል ስትራቴጂ ሠነድና የመተዳደሪያ ደንብ ማሻሻያ ረቅቂ መርምሮ እንዲጸድቅ ማድረጉንም ገልጧል።

የመለስ መንግስት ግንቦት7ትን በአሸባሪ ድርጅትነት መፈረጁ ይታወሳል። በቅርቡ ደግሞ በንቅናቄው ላይ ተደጋጋሚ የሆነ የፕሮፓጋንዳ ዘመቻ ማካሄዱ ይታወቃል።

ንቅናቄው የመለስን መንግስት በሁለገብ ትግል አስገድዶ ወደ ድርድር ለማምጣት፣ ወይም ለማስወገድ እና የሽግግር መንግስት የመመስረት አላማ እንዳለው ገልጧል።