ግሎባል አልያንስ ለደቡብ ክልል ተፈናቃዮች ድጋፍ አደረገ

(ኢሳት ዲሲ–ነሐሴ 7/2010) ትብብር ለኢትዮጵያውያን መብት (ግሎባል አልያንስ) ለደቡብ ክልል ተፈናቃዮች የግማሽ ሚሊየን ብር ድጋፍ  አደረገ።

ከኦሮሚያ ክልል ጉጂ ዞን  ለተፈናቀሉት የጌዲዮ ተወላጆች  እንዲሁም  በሐዋሳና ጉራጌ ዞን በተፈጠረው ግጭት  ለተፈናቀሉት ዜጎች  የተላከው ድጋፍ በሰማያዊ ፓርቲ አመራሮች አማካይነት  ለተፈናቃዮቹ መድረሱን መረዳት ተችሏል።

በውጭ ሃገር የሚገኙ ኢትዮጵያውያን ያቋቋሙትና በአክቲቪስት ታማኝ በየነ የሚመራው ግሎባል አልያንስ ከላከው የግማሽ ሚሊዮን ብር ድጋፍ ለጌዲዮ ተፈናቃዮች 300 ሺህ ብር ሲሰጥ ፣ቀሪው 200 ሺህ ብር ለወላይታ እና ጉራጌ ዞን ተፈናቃዮች መድረሱም ተመልክቷል።

ግሎባል አልያንስ በኦሮሚያ እና በአማራ ክልል በመንግስት ሃይሎች  ጥቃት የደረሰባቸውን  ዜጎች ጨምሮ ከተለያዩ ሥፍራዎች ለተፈናቀሉ ወገኖች ድጋፍ ሲያደርግ ቆይቷል።