ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ እስራቱን ቢጨርስም ከወህኒ ቤት አለመፈታቱ ታወቀ

(ኢሳት ዜና–ጥቅምት 3/2010) የሶስት አመታት እስራት ተፈርዶበት ከ2007 ጀምሮ በወህኒ ቤት የሚገኘው ጋዜጠኛው ተመስገን ደሳለኝ እስራቱን ቢጨርስም ከወህኒ ቤት አለመፈታቱ ታወቀ።

ጋዜጠኛ ተመስገን የሶስት አመታት እስራቱን ጥቅምት 3/2010 ሙሉ በሙሉ መጨረሱንም ማረጋገጥ ተችሏል።

በፍትህ ጋዜጣና በተለያዩ የፕሬስ ውጤቶች ላይ በቀረበው ጽሁፍ አመጽ በመቀስቀስ ተወንጅሎ የሶስት አመታት እስራት ተፈርዶበት በመስከረም 2007 ቃሊቲ ወህኒ የወረደው ተመስገን ደሳለኝ ያለፉትን ሶስት አመታት በይበልጥ ያሳለፈው በዝዋይ ወህኒ ቤት እንደሆነም ተመልክቷል።

በሀገሪቱ ህግ መሰረት እስረኛው ከተፈረደበት ሁለትሶስተኛውን ካጠናቀቀና በወህኒ ቤት ውስጥ የተለየ ነገር ካልፈጸመ አንድሶስተኛው የእስር ጊዜው ተነስቶለት በአመክሮ እንደሚፈታ ይታወቃል።

ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ ይህንንም መብት በመነፈጉ ለተጨማሪ አንድ አመት ወህኒ ቤት ውስጥ ቆይቷል።

የአመክሮ መብቱ ለምን እንደተነፈገው ግን እንዳልተገለጸለት መረዳት ተችሏል።

ያለበቂ ምክንያት ለተጨማሪ አንድ አመት በወህኒ መቆየቱ የተገለጸው ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ በፍርድ ቤቱ ውሳኔ መሰረት የሶስት አመታት እስራቱን ሙሉ በሙሉ ጥቅምት 3/2010 ላይ ቢያጠናቅቅም ይህ ዘገባ እስከተጠናቀረበት አርብ ምሽት ድረስ ከእስር አልተለቀቀም።