ጀርመናዊው የአዳማ ዩኒቨርስቲ ዲን ስራቸውን ለቀቁ

ሰኔ ፳፱ (ሃያ ዘጠኝ) ቀን ፳፻፬ ዓ/ም

ኢሳት ዜና:-አዳማ ዩኒቨርስቲን በጀርመን የትምህርት አደረጃጀት መሰረት ሞዴል ዩኒቨርስቲ ለማድረግ የተጀመረው እንቅስቃሴ ተቋርጧል። ፕሮፌሰር ፒተር ላንግፊልድ የጀርመን መንግስት የውጭ ትምህርት ግንኙነት ( ዳድ) ግፊት ወደ ኢትዮጵያ ከሁለት አመት ከስድስት ወራት በፊት ቢያቀኑም፣ የሶስት አመት የኮንትራት ውላቸው እያለ ከዩኒቨርስቲው እንዲለቁ ተደርጓል። ከእርሳቸው ጋር አብረው የተጓዙ ሌሎች 5 ጀርመናዊያንም ዩኒቨርስቲውን ለቀው እንዲወጡ ተደርጓል። መንግስት በምትካቸውም የደቡብ ኮሪያን ምሁራን ተክቷል። በዚህም የተነሳ አዳማ ዩኒቨርስቲን በጀርመን የትምህርት ስርአት በመቅረጽ ሞዴል ለማድረግ የተጀመረው ጥረት ተቋርጧል።

የ68 አመቱ ዲን ኢትዮጵያን የሚወዷት ቢሆንም ፣ በትምህርት ስርአቱ እና በአጠቃላይ በኢትዮጵያ የልማት ጉዞ ላይ አዝነው መመለሳቸውን ተናግረዋል። ከሁሉም በላይ ጀርመናዊያን በ20 ከፍተኛ ዩኒቨርስቲዎች የሚመረቁ ተማሪዎችን በ2015 ከ150 ሺ ወደ 450 ሺ ለማሳደግ የሚደረገውን ሙከራ ተቃውመዋል። የጀርመን መንግስት የውጭ ትምህርት ትብብር በልማት ትብብር ስም የሚያካሂደውን ተገቢ ያልሆነ ስራም ተችተዋል። የጀርመን መንግስት የሚሰጠው እርዳታም ተገቢ አለመሆኑን እና እንደገና መጠናት እንዳለበት ምሁሩ ተናግረዋል።

የስዊድን ጋዜጠኞች መታሰራቸውን ተከትሎ ጀርመን ለኢትዮጵያ የምትሰጠውን እርዳታ በተወሰነ መጠን መቀነሷ የኢትዮጵያን መንግስት አስቆጥቶ ለበቀል አነሳስቶት ሊሆን ይችላል የሚሉ አስተያየቶች አሉ።

ከከፍተኛ ዩኒቨርስቲዎች የሚመረቁ ተማሪዎች ትምህርታቸውን ጨርሰው ኮብል ስቶን በማንጠፍና በጎዳና ተዳዳሪነት እየተሰማሩ መሆኑ መዘገቡ ይታወሳል። መንግስት የሚሊኒየም የልማት ግቦችን አሳካለሁ በሚል የአገሪቱ ኢኮኖሚ ሊሸከመው ከሚችለው በላይ ተማሪዎችን በለብለብ ትምህርት እያሰለጠ መሆኑ እያስተቸው ይገኛል።

___________________________________________________________________________________________________________________________________________________

ESAT is the first independent Ethiopian satellite service tasked to produce accurate and balanced news and information, as well as other entertainment, sports and cultural programming created for and by Ethiopians.

ESAT is committed to the highest standards of broadcast journalism and programming and will strive to provide an outlet of expression to all segments of the diverse Ethiopian community worldwide