ያለው አማራጭ ሕገ-መንግስቱን ማሻሻል ብቻ ነው ሲሉ አንጋፋው የሕውሀት ታጋይ አቶ ስብሐት ነጋ ገለጹ

ታህሳስ ፲፯ (አስራ ሰባት) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም

ኢሳት ዜና:-አቶ ስብሐት ነጋ በዛሬው ዕለት አዲስ አበባ ከተማ ለንባብ ለበቃው ሰንደቅ ጋዜጣ በሰጡት ቃለ ምልልስ የመለስ ራዕይ የሚባለው ነገር ትክክል እንደማይመስላቸውና ያለው የጋራ ራዕይ መሆኑን ገልጠዋል::

ሦስት ምክትል ጠ/ሚኒስትር መሾም ያስፈለገው ክፍት የአመራር ቦታ ስለነበር እንደሆነ ያወሱት አቶ ስብሐት ነጋ: መደረግ የነበረበት ነገር መከናወኑን አስረድተዋል::

ይህ እርምጃ ሕገ-መንግስቱን ይጥሳል በሚል የሚነሳውን ተቃውሞ በተመለከተ እኔ የማውቀው ነገር የለም ያሉት አቶ ስብሐት ነጋ ሕገ-መንግስቱ ከተጣሰም ያለው አማራጭ ሕገ-መንግስቱን ማሻሻል ወይንም ሌላ አማራጭ መፈለግ እንጂ አዲሱ አደረጃጀት መቀጠል አለበት ብለዋል::

ሕዝባዊ ወያኔ ሐርነት ትግራይ (ሕውሀት)ን ከ1971 እስከ1981 በመሪነት ያገለገሉትና አሁን ይፋዊ የሆነ የፓርቲ አመራር ስፍራ የሌላቸው አቶ ስብሐት ነጋ በሐገሪቱ ፖለቲካ ውስጥ ተጽዕኗቸው የጎላ መሆኑ እየተገለጸ ይገኛል:: በተለይ የአቶ በረከት ሥምዖን ሚና ከቀነሰ ወዲህ ይበልጥ እያንሰራሩ መሆናቸው የተገለጸው አቶ ስብሐት ነጋ በዚህ ረገድ ለተነሳባቸው ጥያቄ እኔ ተራ አባል ነኝ ያለ ሃላፊነቴ ምንም የምሰራው ነገር ያለም ብለዋል::

እኔ ሥርዓት ከጣስኩ ከግንቦት 7: ኦብነግ እና ኦነግ በምን እለያለሁ:: በማለት ጠይቀው ምንም ሚና የለኝም የሚል ምላሽ ሰጥተዋል::

የአቶ መለስ ራዕይ በሚል የሚነሳውን በተመለከተም “በግለሰብ ብቻ የተቀመጠ ራዕይ ሳይሆን የሁላችንም ዕሴት የሆነ የጋራ ራዕይ ነው” በሚል ምላሽ ሰጥተዋል:: ሆኖም አቶ መለስ ወሳኝ ሰው እንደነበሩ በቃለ ምልልሱ አንስተዋል::

በድርጅቱ ውስጥ ክፍፍል ስለመፈጠሩ ለተነሳባቸው ጥያቄ “እስከአሁን በኢሕአዲግ ውስጥ ይሁን በአባል ድርጅቶቹ መከፋፈል የሚባል ነገር  ገጥሞ አያውቅም:: በዚህ ሂደት በተለያዩ መለኪያዎች ለኢሕአዲግ ብቁ ያልሆኑ ሰዎች ተባረዋል ወይንም በራሳቸው ለቀው ወደ ሚመጥናቸው ድርጅት ሔደው ይወድቃሉ” ያሉት አቶ ስብሐት ነጋ “አሁን በኢሕአዲግ ውስጥ የሚታይ የሚሰማ የፖለቲካ ጥያቄ ያለ አይመስለኝም ብለዋል:: ካለም እንዳለፈው ጸጋ ነው:: በአፈጻጸም ዙሪያም ጥያቄዎች ሊኖሩ ይችላሉ” ሲሉ ምላሽ ሰጥተዋል::