የፖለቲካ ድርጅት መሪዎችና የሰብአዊ መብት ተሟጋቾች ከእስር ተለቀቁ

የፖለቲካ ድርጅት መሪዎችና የሰብአዊ መብት ተሟጋቾች ከእስር ተለቀቁ
(ኢሳት ዜና የካቲት 7 ቀን 2010ዓ/ም) ታዋቂውን ጋዜጠኛ እስክንድ ነጋን እንዲሁም የቀድሞውን አንድነት ፓርቲ የህዝብ ግንኙነት ሃላፊ አቶ አንዱላአለም አራጌን ጨምሮ፣ በአገዛዙ ከፍተኛ በደልና ሰቆቃ የተፈጸመባት እማዋይሽ ዓለሙ፣የሙስሊም መፍትሔ አፈላላጊ ኮሚቴ አመራር የሆኑት እነ ኡስታዝ አሕመዲን ጀበል ፣
አርበኞች ግንቦት7 ትን ሊቀላቀል ሲል መንገድ ላይ እንደተያዘ የተነገረለት ብርሃኑ ተክለያሬድ፣የቀድሞ የጋምቤላ ክልል ፕሬዘዳንት አቶ ኦኬሎ አኳይ እና የቀድሞ የፓርላማ አባል አቶ አንዱዓለም አያሌው ፣በኦነግ ስም የተከሠሰችው የዩኒቨርስቲ ተማሪዋ ጫልቱ ታከለ ፣የመኢአዱ መሪ አቶ ማሙሸት አማረና የመላው ኢትዮጵያ ዲሞክራሲያ ፓርቲ ዘሪሁን ገብረ እግዚአብሔር፣ አቶ ክንፈሚካዔል ደበበ ፣አቶ ውብሸት ታዬ ፣አቶ ኦልባና ሊሌሳ እና ሌሎችም የህሊና እስረኞች ተፈተዋል።
ጋዜጠኛ እስክንድ ነጋ እና አቶ አንዱለአም አራጌ መስከረም 3 ቀን 2004 ዓም በደህንነቶች ታፈነው ከተወሰዱ በሁዋላ ያለፉትን 7 አመታት በከፍተኛ ስቃይ አሳልፈዋል። ጋዜጠኛ እስክንድር 18 ዓመት አንዱአለም አራጌ ደግሞ የእድሜ ልክ እስር ተፈርዶባቸው ነበር።
ሁሉም የህሊና እስረኞች ከእስር ቤት ሲወጡ በርካታ ህዝብ አቀባባል አድርጎላቸዋል።
በነ ብርጋዴር ጄነራል ተፈራ ማሞ የክስ መዝገብ ከተከሰሱት መካከል 22ኛ ተከሳሽ የሆነችው እማዋይሽ ዓለሙ ”ወንድሞቼ ካልተፈቱ በስተቀር ብቻዬን ተነጥዬ አልወጣም ።” በማለት በትናንትናው ዕለት ለተፈችዎች የሚሰጥ ስልጠናን እንዳቋረጠች ተነግሯል።
ዛሬ በደረሰን መረጃ መሰረት ከሴት ልጇ ተነጥላ አስከፊ የእስር ቤት ስቃይ ስታሳልፍ የነበረችው ታጋይ እማዋይሽ ከወህኒ ወጥታለች።
እነ አሕመዲን ጀበል የህዝበ ሙስሊሙን የመብት ጥያቄ በማንሳታቸው ሳቢያ የሀሰት የሽብርተኝነት ክስ ተመስርቶባቸው ባለፉት ስድስት ዓመታት በእስር ማሳለፋቸው ይታወቃል።
ከዳር እስከ ዳር በሕዝባዊ ተቃውሞ እየተናጠ ያለው አገዛዝ ባሳለፍነው ሳምንት እነ አሕመዲን ጀበልን ይቅርታ ጠይቀው ከእስር እንዲወጡ ቢነግራቸውም፣ እነሱ ግን የሰራነው በደል ስለሌለ ይቅርታ የምንጠይቅበት ምክንያት የለም በማለት ምላሽ ሰጥጠዋል።
በመኾኑም ኡስታዝ አህመዲን ጀበልን፣ ኡስታዝ በድሩ ሀሰንን እና ኡስታዝ ያሲን ኑሩን ጨምሮ የኮሚቴ አባላቱ በአቋማቸው እንደጸኑ ክሳቸው ተቋርጦ ዛሬ ከእስር ተፈተዋል። እነ አቶ አህመዲን ከእስር ቤት ሲወጡ በርካታ ህዝብ በአጀብ ተቀብሎአቸዋል።
በተመሳሳይ የሰማያዊ ፓርቲ አባል የነበረውና አርበኞች ግንቦት ሰባትን ለመቀላቀል ወደ ኤርትራ ሲያቀና የታሰረው ወጣት ብርሃኑ ተክለ ያሬድም ከእስር ተፈቷል።
ወጣት ብርሀኑና አብረውት የታሰሩት የሰማያዊ ፓርቲ ወጣቶች ፍርድ ቤት ቀርበው የቀረበባቸው ክስ እውነት ስለመሆኑ ሲጠየቁ፦”አዎ፣ ሥርዓቱ በሰላማዊ መንገድ ሊለወጥ ስላልቻለ፣ እንዲሁም መሪው መለስ ዜናዊ ፦ በኃይል እታገላለሁ ለሚል መንገዱን ጨርቅ ያርግለት”በማለታቸው ከግንቦት ሰባት ጋር ተቀላቅለን ለመታገል አምነንበት ስንሄድ ነው የተያዝነው”ማለታቸው ይታወሳል።
እንዲሁም የመኢአዱ ማሙሸት አማረና በሀሰት የሽብርተኝነት ክስ 17 ዓመታት ተፈርዶበት የነበረው የተቃዋሚ ፓርቲ አመራሩ ዘሪሁን ገብረ እግዚአብሔር ክሳቸው ተቋርጦ ከአስከፊው እስር ቤት ወጥተዋል።
ከፕሮፌሰር አስራት ወልደየስ ጋር አስር ዓመታት፣ እንዲሁም በ1997ቱ ምርጫ ከቅንክት መሪዎች ጋር ለሁለት ዓመታት የታሰረው የመኢአዱ ማሙሸት አማረ ፣ ዲሞክራሲያዊት ኢትዮጵያን እውን ለማድረግ ከማለዳው ጀምሮ በግንባር ቀደምትነት ከአገዛዙ ጋር በመተናነቁ በተደጋጋሚ ለእስርና ለንግልት የተዳረገ ታጋይ ነው።
በተመሣሳይ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቱ የ2ተኛ ዓመት የሶሲዮሎጅ ተማሪ በነበረችበት ወቅት በኦሮሞ ነጻነት ግንባር አባልነት ተከሳ ላለፉት አስር ዓመታት በእስር ያሳለፈችው ጫልቱ ታከለም እንዲሁ ክሷ ተቋርጦ ከወህኒ ወጥታለች።
በትናንትናው ዕለት እንዲሁ በሽብርተኝነት ተከሰው የነበሩት የኦሮሞ ፌዴራሊስት ኮንግረስ አመራሮች በተመሣሳይ መንገድ ክሳቸው ተቋርጦ መፈታታቸው ይታወሳል።
ኦቦ በቀለ ገርባ፣ ጉርሜሳ አያኖ፣ አዲሱ ቡላላ፣ ደጀኔ ጣፋ፣ ጌቱ ግርማ፣ ተስፋዬ ሊበን እና በየነ ሩዳ ከእስር እንደተለቀቈጅግ በርካታ የኾነ የአዳማ ሕዝብ አደባባይ በመውጣት ደማቅ አቀባበል አድርጎላቸዋል።