የፖለቲካ እስረኞች ከ15 እስከ 18 አመታት የእስር ጊዜ ተፈረደባቸው

(ኢሳት ዲሲ–ጥር 3/2010)

በኢትዮጵያ 33 የፖለቲካ እስረኞች ከ15 እስከ 18 አመታት የእስር ጊዜ ተፈረደባቸው።

የፊደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 19ኛ ወንጀል ችሎት በእነ ሚፍታህ ሼህ ስሩር የክስ መዝገብ  በግንቦት 7 የተከሰሱ 33 ግለሰቦች ላይ የፍርድ ውሳኔ ሰጥቷል።

ግለሰቦቹ በፖለቲካ አስተሳሰባቸው በሽብርተኝነት ስም የተከሰሱ መሆናቸው ነው የተነገረው።

በክስ መዝገቡ ከተካተቱት ተከሳሾች ቀሪዎቹ ክደው በመከራከራቸው የመከላከያ ምስክር ለማቅረብ ቀጠሮ እንደተሰጣቸው ከሀገር ውስጥ ያገኘነው መረጃ ያመለክታል።

በኢትዮጵያ ያለው አገዛዝ የፖለቲካ ምህዳሩን ለማስፋት ሲባል እስረኞችን እለቃለሁ እያለ በሌላ በኩል ከፍተኛ የእስር ቅጣት እንዲወሰን ማድረጉ ብዙዎችን ግራ ያጋባ ነገር ሆኗል።

በሕወሃት የሚመራው አገዛዝ የፖለቲካ እስረኞችን እለቃለሁ በሚል ለሕዝብ ቃል ከገባ በኋላ አንድም እስረኛ ለቆ አያውቅም።