የጭልጋ ወረዳ አመራሮች ታሰሩ

(ኢሳት ዲሲ–ሐምሌ 27/2010) የመንግስትን መዋቅር በመጠቀም በአማራና ቅማንት ማህበረሰቦች መካከል ግጭት ለመፍጠር የተንቀሳቀሱ 7 የጭልጋ ወረዳ አመራሮች መታሰራቸው ታወቀ።

በአማራ ክልል ፖሊስ የተያዙት አመራሮች በህወሀት የሚደገፈውን የቅማንት ኮሚቴ በማገዝ በአካባቢው ግጭት እንዲፈጠር ማድረጋቸውን የደረሰን መረጃ ያመለክታል።

በግጭቱ የተነሳ በጭልጋ ወረዳ አይከል ዙሪያ የመንግስት መስሪያ ቤቶችን ጨምሮ የንግድ ተቋማት እንደተዘጉም ለማወቅ ተችሏል።

ለአንድ ሳምንት ተዘግቶ የነበረው የአይከል መንገድ ትላንት መከፈቱ ታውቋል።

የቅማንትን የመብት ጥያቄ እንደሽፋን በመጠቀም ግጭት እየፈጠረ ነው በሚል የሚወነጀለው የህወሀት ቡድን አዲስ ዙር ቀውስ በአከባቢው መፍጠሩን የኢሳት ምንጮች ይገልጻሉ።

በህወሀት የተደራጀው የቅማንት የመብት ኮሚቴ በጭልጋ ወረዳ ዳግም ውጥረት ማንገስ ከጀመረ ቭከአንድ ወር በላይ እንደሆነም ይነገራል።

ባለፉት ሁለት ሳምንታት እንደገና ያገረሸው ውጥረት በጭልጋ ወረዳ በተለያዩ አከባቢዎች ግጭት እንዲከሰት ማድረጉን የደረሰን መረጃ አመልክቷል።

የአይከል ከተማ በቅማንት በሚደራጀው አዲስ መዋቅር ስር ለሚገኘው አስተዳደር ዋና ከተማ እንድትሆን በሚል አዲስ የግጭት አጀንዳ የከፈተው ኮሚቴው ባሰማራቸው ታጣቂዎች አማካኝነት ጥቃት መክፈቱን ነው የአከባቢው የኢሳት ምንጮች የሚገልጹት።

በጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድና በአመራራቸው የመጣውን ለውጥ ለመቀልበስ ውስጥ ውስጡን እየሰራ ነው እንደሆነ የሚነገርለት የህወሀት ቡድን የቅማንትን የመብት ጥያቄ እያራገበው ነው ተብሏል።

ለዚህም አቶ በረከት ስምዖን ወደ ጭልጋ አከባቢ በተደጋጋሚ ሲመላለሱ እንደነበረ የሚጠቅሱት የኢሳት ምንጮች የቅማንት ኮሚቴን በመሰብሰብ ሲያስተባብሩ መታየታቸውንም ይጠቅሳሉ።

በህወሀት የተደራጀውና ታጣቂዎች ያሉት የቅማንት ኮሚቴ በተለይ በአይከል ከተማ የግለሰቦችን ንብረት በማውደም ከፍተኛ ጉዳት እያደረሰ መሆኑን ለማወቅ ተችሏል።

ካለፈው ሳምንት ጀምሮ በጭልጋ ወረዳ አንዳንድ አከባቢዎች በተኩስ የታገዘ ጥቃት ተከፍቶ ለጊዜው ቁጥራቸው በውል ያልታወቁ ሰዎች መገደላቸው ተገልጿል።

በጭልጋ ወረዳ ባለፉት ሁለት ሳምንታት መንገዶች፡ ትምህርትና መስሪያ ቤቶች፡ የንግድ ተቋማት ተዘግተው እንደነበረም ታውቋል።

ውጥረቱን ለማርገብ በአማራ ክልል መንግስት የተዘጋጀውን ህዝባዊ ስብሰባም የቅማንት ኮሚቴ ባሰማራቸው ግለሰቦች አማክኝነት ተበጥብጦ መበተኑን የደረሰን መረጃ አመልክቷል።

የአማራ ክልላዊ መንግስት በጭልጋ ወረዳ የተከሰተውን ግጭት ለመቆጣጠር ከትላንት ጀምሮ እርምጃ በመውሰድ ላይ መሆኑን ነው ለማወቅ የተቻለው።

በውይይትና ህዝባዊ ስብሰባዎች ቀውሱን ለማስወገድ የተደረገው ጥረት ውጤታማ ባለመሆኑ የክልሉ መንግስት ወደ አከባቢው ጸጥታ አስከባሪዎችን አሰማርቷል።

በዚህም መሰረት የመንግስትን መዋቅር ህወሀት ካደራጀው የቅማንት ኮሚቴ ጋር በመሆን ግጭት እንዲቀሰቀስ አድርገዋል የተባሉ የጭልጋ ወረዳ ሰባት አመራሮችን በቁጥጥር ስር እንዲውሉ ተደርገዋል።

እነዚህ አመራሮች በወረዳው አስተዳደርና በፖሊስ ጽ/ቤት ውስጥ ቁልፍ ስልጣን ይዘው ግጭቱን ሲያባብሱና ሲያስተባብሩ የተደረሰባቸው እንደሆነ ተገልጿል።

የቅማንት የመብት ኮሚቴ በሚል ራሱን የሚጠራው አካል ዋና ጽ/ቤቱ በመቀሌ የሚገኝ ሲሆን ከህወሀት በሚሰጠው ቀጥተኛ የገንዘብና የጦር መሳሪያ ድጋፍ ግለሰቦችን እየመለመለ በጭልጋ አከባቢ ግጭት ሲቀሰቅስ እንደነበረ መዘገቡ የሚታወስ ነው።